ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ የሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበርን ጎበኙ

የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ  የሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበርን ጎብኝተዋል፡፡

በጉብኝቱም ወቅት ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ እንደገለጹት፥ ማህበሩ በርካታ ወላጅ አልባ ህጻናትና እናቶችን በማሰባሰብ አስቸጋሪ በሆነ የሥራ ሁኔታ ውስጥ የሚያከናውናቸው በጎ ተግባራት የሚደነቁ ናቸው።

“ኢትዮጵያውያን ከተባበርን ብዙ መስራትና ማድረግ እንደምንችል ሙዳይ የበጎ አድራጎት ማህበር ጥሩ ምሳሌ ነው” ያሉት ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ፥ “ሌሎች ችግሮቻችንንም እንዲሁ በተባበረ እና በተቀናጀ መንገድ ለመቅረፍ ብንነሳ ብዙ ነገር ከአቅማችን በላይ አይሆንም” ሲሉም ተናግረዋል።

ለዚህ ስኬት ደግሞ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የሚችለውን ሁሉ እንዲያደርግ ነው መልዕክታቸውን ያስተላለፉት፡፡

በማህበሩ ድጋፍ የሚሰጣቸውን ህጻናት፤ወላጆች እና የማህበሩን ሰራተኞችም ያበረታቱት ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ፥ ማህበሩን ለመደገፍ የሚችሉትን ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማይሉ ገልፀዋል።

ሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ከ19 ዓመት በፊት የተቋቋመ ሲሆን፥ በአሁኑ ወቅትም 614 ልጆች እና 450 እናቶችን በተለያየ ሁኔታ በመደገፍ ላይ ይገኛል።

ከ614 ልጆቹ ውስጥ 150ዎቹ በማህበሩ ግቢ ውስጥ የሚውሉ፣ የሚማሩ እና የሚያድሩ ናቸው፤ እናቶች ደግሞ የሸክላ ቅርጻ ቅርጽ፣ የሽመና እና የልብስ ስፌትን ጨምሮ የተለያዩ ሙያዊ ስልጠናዎች እንዲሰጣቸው ይደረጋል።

ይህም ሆኖ ግን ማህበሩ የተለያዩ ችግሮች ለሥራው እንቅፋት እየሆኑበት መምጣታቸውን ነው የማህበሩ መስራች ወይዘሮ ሙዳይ ምትኩ የገለጹት።

በተለይም ደግሞ ሌሎች ወጪዎች እንዳሉ ሆነው ሥራውን የሚያከናውነው በየወሩ 160 ሺ ብር በሚከፈልበት የኪራይ ቤት መሆኑ አጠቃላይ የማህበሩን እንቅስቃሴ አስቸጋሪ ማድረጉን አመልክተዋል።

ይህንንም ሁኔታ ለማስካከል የመሬት ጥያቄ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቀርቦ ቢፈቀድም እስካሁን ድረስ መቋጫ ሊያገኝ አለመቻሉም ጠቁመዋል፡፡     (ምንጭ ፡ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤት)