ሜዲትራኒያን ባሕር ላይ የስደተኞችን ህይወት የሚታደገው ቡድን ሥራውን ጀመረ

በሊቢያ በኩል በትናንሽ ጀልባዎች ወደ አውሮፓ የሚሻገሩ ስደተኞችን የሚታደገው የበጎ አድራጎት የነፍስ አድን ድርጅት ሥራውን በአውሮፓ መንግሥታት ጫና እንዲያቆም ከተደረገ በኋላ እንደገና ጀመረ።
ኤስኦኤስ ሜዲትራኒያኔ በሚባል የሚታወቀው የነፍስ አድን በጎ አድራጎት ቡድን ሥራውን እንደገና የጀመረው ኦሺን ቫይኪንግ በተባለች አዲስ መርከብ ሲሆን፣ መርከቧ የኖርዌይ ሰንደቅ ዓላማን ታውለበልባለች።
መርከቧ የነፍስ አድን ቡድኑ አጋር ከሆነው የድንበር የለሽ ሃኪሞች ቡድን የተወጣጡ ዘጠኝ የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ 31 ሰራተኞችን ይዛለችም ነው የተባለው።
ኤስኦኤስ ሜዲትራኒያኔ የነፍስ አድን ቡድን ቀደም ሲል በሜዲትራኒያን ባሕር ላይ አሰማርቷት በነበረችው አኳሪየስ በተባለቸው መርከብ አማካይነት ሲያከናውን የነበረው ሥራ ለማቋረጥ ተገዶ የነበረው ወደ ጣሊያን እንዳይገባ በመከልከሉ ነበር።
የኤስኦኤስ ሜዲትራኒያኔ መሰራቾች ከሆኑት መካከል አንዷ ሶፊ ቤዩ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ሥራቸውን እንዲጀምሩ የተገደዱት በአሁኑ ወቅት በባሕር ላይ በአደገኛ ሁኔታ የሚጓዙ ስደተኞችን ለመታደግ የሚሰራ በጎ አድራጎት ቡድን በአካባቢው ስለሌለ መሆኑን ተናግረዋል።
ከአራት ዓመት በፊት የተቋቋመው ይህ የነፍስ አድን ቡድን እስካሁን 30 ሺህ የሚደርሱ ሰዎችን ህይወት ባሕር ላይ ከሚያጋጥም አደጋ ማትረፉን ገልጸው፤ ወታደራዊ መርከቦችን ጨምሮ ሌሎች መርከቦችም ተጨማሪ የበርካታ ስደተኞችን ህይወት መታደጋቸውን ተናግረዋል።
"ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ የነፍስ አድን ሥራውን በማከናወን በኩል ክፍተት አለ፤ በቂ ባይሆንም መስራት ያለብንን እንሰራለን፤ መንግሥታት የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት ሳይወጡ ሲቀር ማድረግ የምንችላውን እናደርጋለን" ብለዋል ሶፊ።
ከአውሮፓ መንግሥታት የሚገጥማቸውን ተቃውሞ በተመለከተም የዓለም የባሕር ሕግ ከየትኛውም ፖለቲካዊ ጉዳይ በላይ የሰውን ህይወት ማዳንን ቅድሚያ ስለሚሰጥ የቡድናቸውን አቋም እንደሚደግፍ ጨምረው ይናገራሉ።
በዚህ ዓመት ጥር ወር ላይ የወጣ የተባበሩት መንግሥታት ሪፖርት ባለፈው የፈረንጆች ዓመት በየቀኑ የሜዲትራኒያን ባሕር ለማቋረጥ የሚሞክሩ የስደስት ስደተኞች ህይወት ያልፍ እንደነበር አመልክቷል።
የዓለም የስደተኞች ድርጅት እንደሚለው በዚህ የፈረንጆች ዓመት እስካሁን ድረስ ቢያንስ 426 ሰዎች የሜዲትራኒያን በሕርን ለማቋረጥ ሲሞክሩ ህይወታቸው አልፏል። (ምንጭ፡-ቢቢሲ)