ትራምፕ አዲሱን የጃፓን ንጉሥ በማግኘት የመጀመሪያው መሪ ሆኑ

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የጃፓኑን ንጉሥ ናሩሂቶ በማግኘት የመጀመሪያው መሪ ሆኑ።

ለአራት ቀናት ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ጃፓን የሚገኙት ትራምፕ፣ ቶኪዮ የሚገኘው በንጉሡ ቤተመንግሥት ተገኝተው እጅ ነስተዋል።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ ንጉሡን ከማግኘታቸው አስቀድመው "ትልቅ ክብር" ነው ብለው ነበር።

አጼ ናሩሂቶ በዚህ በፈረንጆች ግንቦት ወር አባታቸው ዙፋናቸውን በፈቃደኝነታቸው በመልቀቃቸው ነበር ንግሥናቸውን የተቀበሉት፤ ይህም በጃፓናውያን ንጉሣውያን የመቶ አመታት ታሪክ ዙፋኔን ልልቀቅ ያሉ ንጉሥ አስብሏቸዋል።

"እንዲህ አይነት ነገር ከተከሰተ 200 ዓመት ያህል አልፎታል" ብለዋል ትራምፕ፤ ንጉሱ ሥልጣናቸውን የተረከቡበትን መንገድ በማንሳት "አሜሪካን ወክዬ በፊታቸው መገኘቴ ትልቅ ክብር ነው" ሲሉም ተደምጠዋል።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ባለቤታቸው ሜላኒያ፣ በጃፓን ክቡር ዘበኛ አቀባበል የተደረገላቸው ሲሆን በርካቶችም የሁለቱን ሀገራት ባንዲራ እያውለበለቡ የእንኳን ደህና መጡ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።

የሳምንቱ መጨረሻንም ከጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ ጋር ጎልፍ ሲጫወቱና የጃፓን ባህላዊ ስፖርት የሆነውን ሱሞ ሲመለከቱ አሳልፈዋል።

ሁለቱ ባለስልጣናት ዛሬ ተገናኝተው ከሰሜን ኮሪያ ጋር ስላለው ግንኙነትና ስለ ንግድ ያወራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በቻይናና በአሜሪካ መካከል የተፈጠረው መቃቃር ጃፓንንም እየጎዳት ስለሆነ ይህንንም ማንሳታቸው አይቀርም ተብሏል።

በኋላም ቤተሰቦቻቸው በሰሜን ኮሪያ የታገቱባቸው ጃፓናውያንን በማግኘት ያነጋግራሉ። ጃፓናውያኑ የታገቱት የሰሜን ኮሪያ ሰላዮችን ጃፓንኛ ለማስተማር ሲሆን ይሀም ሁለቱን ሀገራት አይንና ናጫ አድርጓቸው መክረሙ ይታወቃል።

ሰሜን ኮሪያ በ1970ዎቹና ሰማኒያዎቹ 13 ጃፓናውያንን ማገቷን አምና አምስቱን በ2002 መልሳለች። ቀሪዎቹ መሞታቸው ቢነገርም ጃፓናውያን ግን ይህንን አምነው መቀበል አልፈለጉም።

(ምንጭ፡-  ቢቢሲ)