ቦሪስ ጆንሰን የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ

ተሰናባቿን ቴሬዛ ሜይን በመተካት ቦሪስ ጆንሰን የወግ አጥባቂ ፓርቲ መሪ ተደርገው የተመረጡ ሲሆን ቀጣዩም የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል።
ቦሪስ ጆንሰን 92ሺ 153 ድምፅ ያገኙ ሲሆን ተወዳዳሪያቸው ጄረሚ ሃንት 46ሺ656 ድምፅ አግኝተዋል።
የለንደን ከተማ ከንቲባ የነበሩት ቦሪስ ጆንሰን ካሸነፉ በኋላም ብሬግዚትን እንደሚያሳኩና የሃገሪቷንም አንድነት እንደሚያስጠብቁ ተናግረዋል።
በለንደን በሚገኘው የንግሥት ኤልሳቤጥ ማዕከል ንግግር ያደረጉት የዩናይትድ ኪንግደም ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር "የህዝቡን ስሜት አነቃቃለሁ" ብለዋል።
በጥቅምት መጨረሻ ብሬዚትን እንደሚያሳኩ ተናግረው "በራስ የመተማመን መንፈሳችንን እንደገና እንመልሰዋለን" ብለዋል።
አክሎም ተሰናባቿን ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬዛ ሜይን በርሳቸው ካቢኔ ውስጥ ማገልገላቸውን ትልቅ እድል ነው ብለዋል። ቴሬዛ ሜይ በበኩላቸው የደስታ መልዕክታቸውን አስተላልፈው ድጋፋቸውንም እንደሚለግሱ ተናግረዋል።
በብሬግዚት ፖሊሲያቸው ምክንያት ሥልጣን ለመልቀቅ የተገደዱት ቴሬዛ ሜይ ዛሬ የመጨረሻ የካቢኔ ስብሰባቸውን ይመራሉ።
የሥራ መልቀቂያ ደብዳቤያቸውንም ነገ በይፋ ለንግስት ኤልሳቤት ያቀርባሉ።
ቴሬዛ ሜይን የሚተኩት ጠቅላይ ሚንስትር ቦሪስ ጆንሰን ነገ የንግስቲቷ መኖሪያ በሆነው ባኪንግሃም ቤተ-መንግሥት በሚደረግ ሥነ-ስርዓት ሥልጣኑን ይረከባል።
የቢቢሲ የፖለቲካ አርታኢ ሎውራ ኩንስበርግ እንደምትለው ከሆነ፤ ዛሬ በዌስትሚንስትር አሸናፊ የመሆነ ሰፊ እድል የተሰጠው ለቀድሞ የለንደን ከንቲባ እና የዩናይትድ ኪንግደም የውጪ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ቦሪስ ጆንሰን ሲሆኑ በትንበያውም መሰረት አሸንፈዋል።
የወግ አጥባቂ ፓርቲ አባላት ቀጣዩ የፓርቲው መሪ እና የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚንስትር ማን እንደሚሆነ ለመወሰን ባለፉት ሁለት ሳምንታት ድምጽ ሲሰጡ ቆይተዋል። ዛሬ ከሰዓት የድምጽ አሰጣጥ ሥነ-ስርዓቱ ተጠናቋል።
ቦሪስ ጆንሰን ዩናይትድ ኪንግደም ከአውሮፓ ህብረት እንድትለይ ፍላጎት የነበራቸውና ሕዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ ሲቀሰቅሱ የነበሩ ፖለቲከኛ ናቸው።
ቴሬዛ ሜይ ሥልጣናቸውን እንደሚለቁ ይፋ ካደረጉ በኋላ፤ እሳቸውን ሊተኩ የሚችሉ 10 ዕጩዎች ቀርበው ነበር። ከአስሩ እጩዎች ቦሪስ ጆንሰን ከ50 በመቶ በላይ የድጋፍ ድምጽ አግኝተው እንደነበረ ተነግሯል።
የወግ አጥባቂ ፓርቲ ኃላፊዎች ቦሪስ ጆንሰን ዩናይትድ ኪንግደም ከአውሮፓ ህብረት የምትለያይበትን የተሻለ መንገድ ሊቀይሱ ይችላሉ የሚል ተስፋ አላቸው።
በአሁኑ ሰዓት የዩናይትድ ኪንግደም የውጪ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ የሆኑት ጄሬሚ ሃንት፤ በአራት ወራት ውስጥ ከአውሮፓ ህብረት ጋር ከስምምነት በመድረስ ለብሬግዚት መፍትሄ እንደሚሰጡ ተናግረዋል። (ምንጭ፡-ቢቢሲ)