መንግስት የጁንታውን ርዝራዦች የትግራይ ህዝብ አሳልፎ እንዲሰጥ ያቀረበውን ጥሪ በመቀበል አሳልፎ ሊሰጥ ይገባል- ዶ/ር አረጋዊ በርሄ

መንግስት የጁንታውን ርዝራዦች የትግራይ ህዝብ አሳልፎ እንዲሰጥ ያቀረበውን ጥሪ በደስታ በመቀበል ለራሱ ሰላም እና ደህንነት ሲል አሳልፎ ሊሰጥ ይገባል ሲሉ የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር አረጋዊ በርሄ ገለጹ፡፡

የፓርቲው ሊቀመንበር ከዋልታ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፣ በሀገር ላይ ክህደት የፈጸመው ጁንታ ከምንም እና ከማንም በላይ ሲጨቁነው እና ሲዘርፈው የኖረው የትግራይን ህዝብ ነው፡፡

በትግራይ ክልል የነበሩ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ህገ መንግስቱ በሚፈቅድላቸው መንገድ በክልሉ መንቀሳቀስ እንዳይችሉ ጽንፈኛው የትህነግ ቡድን አፈና ሲያደርግባቸው መቆየቱን የገለጹት ዶ/ር አረጋዊ፣ አሁን ላይ ግን ምቹ መደላድል ይፈጠራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን ብለዋል፡፡

አቶ ዮሃንስ ሃይሉ

የትግራይ ተወላጅ የሆኑት አቶ ዮሃንስ ሃይሉ በበኩላቸው፣ አስፈላጊ በሆነው መንገድ ሁሉ በክልሉ ከተቋቋመው ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር በጋራ እንደሚሰሩ ገልጸው፤ የህወሓት ጁንታው ቡድን ላለፉት ረጂም አመታት ሲጨቁነው ከቆየው ህዝብ ውስጥ ተሸሽጎ እንዳለና ይህን ጁንታ በማጋለጥ የትግራይ ህዝብ አኩሪ ታሪክ ሊሰራ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደሩ እያከናወነ ያለው ስራ የሚደነቅ እንደሆነና በቀጣይም ጠንከር ያሉ የቤት ስራዎች የሚጠብቅ በመሆኑ እያንዳንዱ የትግራይ ተወላጅ ከገዜያዊ አስተዳደሩ ጎን ሊቆም እንደሚገባም ጠይቀዋል፡፡

ከሁለት አስርት አመታት በላይ በኢትዮጵያ እና በትግራይ ህዝብ ጫንቃ ላይ ተቀምጦ እንደካንሰር ራሱን በማስፋፋት ህዝቡን ሲበዘብዝ የኖረው የህወሓት ዘራፊ ቡድን ህዝባዊ በሆነው የመከላከያ ሰራዊት ድል ተደርጎ የትግራይ ህዝብ የሰላም አየር መተንፈስ ከጀመረ  ሳምንታት ተቆጥሯል፡፡

መንግስት በክልሉ ያቋቋመው ጊዘያዊ አስተዳደርም ህበረተሰቡን በማወያየት ስራውን የጀመረ ሲሆን፣ በራስ ወዳዱ ጁንታው ቡድን የተበላሸውን የመልካም አስተዳደር ችግር ለማስተካከል ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡

(በሜሮን መስፍን)