በሀገር ደረጃ የሴቶችን ተጠቃሚነትና ተሳታፊነትን ለማጎልበት በትኩረት እየተሰራ ይገኛል- ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ

መጋቢት 18/2013 (ዋልታ) – ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ  በሀረሪ ክልል የሚገኘውን የፊስቱላ ህክምና መስጫ ማዕከል  እንዲሁም ኢናይ አቢዳ የእደ ጥበብ ኮሌጅ እና አብደላ ሸሪፍ የግል ሙዚየምን ጎብኝተዋል፡፡

እንዲሁም በሀረማያ ዩኒቨርሲቲ በመገኘት አእምሮ የማጎልበት የድጋፍ እና ክትትል ስራ (ሜንቶርሺፕ) ፕሮግራም አስጀምረዋል፡፡

በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ የሴቶችን ተጠቃሚነትና ተሳታፊነትን ከማጎልበት አንፃር በመልካም ጎዳና ላይ ትገኛለች ያሉ ሲሆን በተለይም በከፍተኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ሴቶች አካታችና ለሴት ተማሪዎች ምቹ እንዲሆን ከማድረግ አንፃር በትኩረት መንቀሳቀስ ይገባል ብለዋል፡፡

በተለይ ኢኮኖሚያዊ አቅማቸው አነስተኛ ለሆኑ የዩኒቨርሲቲ ሴት ተማሪዎች በዘላቂነት የንጽህና መጠበቂያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ ስለመሆኑ አንስተዋል፡፡

በተጨማሪም  ጥሩ ውጤት  ያላቸው ሴት ተማሪዎች ሌሎች ሴት ተማሪዎችን ለመደገፍና ለማብቃት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን የበለጠ ማጠናከር አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

ፕሬዝዳንቷ በክልሉ በነበራቸው በስራ ጉብኝት በክልሉ የሚገኘውን የፊስቱላ ህክምና መስጫ ማዕከል የተመለከቱ ሲሆን በክልሉ ሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ቢሮ አማካኝነት የተቋቋመውን የማገገሚያ ማዕከልም ስራ አስጀምረዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በክልሉ የሚገኘውን ኢናይ አቢዳ የእደ ጥበብ ኮሌጅ እና አብደላ ሸሪፍ የግል ሙዚየም  ጉብኝተዋል።

ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በሀረሪ ክልል የነበራቸውን የስራ ጉብኝት አጠናቀው ወደ ድሬዳዋ ከተማ መስተዳደር ማቅናታቸውን ከሃረሪ ክልል መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡