መጪው ምርጫ ነፃና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻውን እንደሚወጣ የኦሮሚያ ሴቶች ፌዴሬሽን ገለጸ

የኦሮሚያ ሴቶች ፌዴሬሽን

ሚያዝያ 28/2013 (ዋልታ) – በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደው 6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነፃ፣ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻውን እንደሚወጣ የኦሮሚያ ሴቶች ፌዴሬሽን ገለጸ።

ፌዴሬሽኑ በምርጫ ታዛቢነት ዙሪያ ከኦሮሚያ 20 ዞኖችና ሁሉም የከተማ አስተዳደሮች ለተውጣጡ ሴት አመራሮች በአዳማ ከተማ የአሰልጣኞች ስልጠና መስጠት ጀምሯል።

ዛሬ በተጀመረው የስልጠና መድረክ የተገኙት የኦሮሚያ ሴቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ወይዘሮ አስካለ ለማ እንዳሉት፤ ፌዴሬሽኑ 6ኛ ጠቅላላ ምርጫ ለመታዘብ ከምርጫ ቦርድ ፍቃድ አግኝቷል።

ምርጫው በህዝቡ ዘንድ ተዓማኒነት ያተረፈና ተቀባይነት ያለው እንዲሆን በታዛቢነት ሚናችንን ለመወጣት ዝግጅት እያጠናቀቅን ነው ብለዋል።

በተለይም ህዝቡ ህገ መንግስታዊ መብቱን ተጠቅሞ በወሰደው ካርድ ለሚፈልገው ፓርቲ ድምፅ እንዲሰጥ ከመራጮች ምዝገባ ጀምሮ ሂደቱን እየተከታተሉ መሆኑን ተናግረዋል።

የፖለቲካ ፓርቲዎች ኘሮግራማቸውን የማስተዋወቅ ሂደት ሰላማዊ እንዲሆን፣ የድምፅ አሰጣጡም ግልፅነት የተሞላበትና የህዝብ ድምፅ እንዲከበር ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል።

ችግሮች ቢፈጠሩ እንኳን በሰለጠነ መንገድ የሚፈቱበትን  አቅም ለመፍጠር ጭምር ስልጠናው የጎላ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ወይዘሮ አስካለ አስረድተዋል።

በምርጫው ሂደት የመራጩ ህዝብ ጤንነት እንዲጠበቅ ኮሮናን ለመከላከል የወጣው ፕሮቶኮል መሰረት ባደረገ መልኩ እንዲሆን ትምህርታዊ ግንዛቤ እስከ ቀበሌ ድረስ እንደሚሰጥም አመልክተዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።