ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተለያዩ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ተወያዩ

አምባሳደር መለሰ ዓለም

የካቲት 9/2015 (ዋልታ) የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከተለያዩ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ተወያዩ።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ውይይቱን ያደረጉት እየተካሄደ ባለው የአፍሪካ ኅብረት 42ኛው የሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ ጎን ለጎን ሲሆን ከጋቦን፣ ጋምቢያ፣ ማላዊ፣ ቱኒዝያ እና ሊቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር መወያየታቸው ተገልጿል።

ውይይቱን የተከታተሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለሰ ዓለም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በወቅታዊ የኢትዮጵያ ሰላምና የልማት እንቅስቃሴ ላይ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹ ገለጻ ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

በተጓዳኝም ኢትዮጵያ ለሰላም ትልቅ ቦታ እንዳላት በመጠቆም የሰላም ሥምምነቱን ተግባራዊ በማድረግ በኩል እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎችን በተመለከተ ገለጻ ማድረጋቸውን ተናግረዋል።

እየተከናወኑ ያሉ የመልሶ ማቋቋም እና የመልሶ ግንባታ ሥራዎች እንዲሁም ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ አየተሰራ ስለመሆኑ ማብራሪያ መስጠታቸውንም ነው ያነሱት።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹም ለተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል በማመስገን ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን የዲፕሎማሲ ግንኙነት ለማጠናከር በትኩረት እንደሚሰሩ መግለጻቸውን ተናግረዋል።

በተለይም ደግሞ በቱሪዝም፣ በአየር ትራንስፖርትና በሌሎች ዘርፎች ላይ በትብብር መሥራት የሚቻልባቸው የጋራ ጉዳዮች መኖራቸውን ሚኒስትሮቹ አንስተዋል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የኢትዮጵያ ጥንካሬ የአገራቱ ጥንካሬ እንደሆነ መጥቀሳቸውንና የአፍሪካ ችግር በአፍሪካውያን መፍታት እንደሚቻል ኢትዮጵያ እንደ ምሳሌ የምትወሰድ አገር መሆኗን መጥቀሳቸውን ገልጸዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በትላንትናው ዕለት ከተለያዩ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር መወያየታቸው ይታወሳል።

ሁለተኛ ቀኑን የያዘው የአፍሪካ ኅብረት የሥራ አስፈጻሚዎች ምክር ቤት ስብሰባ ዛሬ ማምሻውን ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።