በሕንድ የአንዲትን ሴት ሁለት ኩላሊት ይዞ የተሰወረ ሀሰተኛ የቀዶ ጥገና ሃኪም እየታደነ ነው

ኅዳር 9/2015 (ዋልታ) የሕንድ ፖሊስ የአንዲትን ሴት ሁለት ኩላሊት ይዞ የተሰወረ ሀሰተኛ የቀዶ ጥገና ሃኪም እያደነ መሆኑ ተገለጸ፡፡

አንዲት ህንዳዊት ሴት ሁለት ኩላሊቷን ሰርቆ የተሰወረ ሀሰተኛ የቀዶ ጥገና ሀኪምን ፖሊስ በፍጥነት በቁጥጥር ስር እንዲያውለው መጠየቋን ኢንዲያን ታይምስ አስነብቧል፡፡

የ38 ዓመቷ ሱኒታ ዴቪ ማህፀኗ በቀዶ ሕክምና እንዲወጣላት ወደ ዶክተር ሪክ ሲንግን ብታመራም ነገር ግን የቀዶ ጥገና ሀኪሙ ኩላሊቷን ሰርቆ ተሰውሯል፡፡

ሀኪሞች ኩላሊቷ እንደተሰረቀ እና አስቸኳይ የህክምና እርዳታ ካላደረገች እንደምትሞት ሲነግሯት በጣም መደንገጧን የገለጸችው ህንዳዊት ሴት ሱኒታ በክርሽና ሜዲካል ሆስፒታል መደበኛ እጥበት እያደረገች ትገኛለች፡፡

የግለሰቧን ህመም የሚከታተሉ ዶክተሮች ህክምና ሳታገኝ አንድ ቀን ካለፈ በህይወት መኖር እንደማትችል ተናግረዋል።