በአሜሪካ የሚኖሩ ወገኖች ለህዳሴ ግድብ የ7,400 የአሜሪካን ዶላር ድጋፍ አደረጉ

ሰኔ 29/2013 (ዋልታ) – በአሜሪካ የሚኖሩ ወገኖች ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የ7ሺህ 400 የአሜሪካን ዶላር ድጋፍ አደረጉ፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ብርሃን ለመስጠት በመቃረቡ ከአሜሪካ የወገን ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉ የተገለጸ ሲሆን፣ ለረጅም ጊዜ የቦስተን ነዋሪ የሆኑት አቶ ሰለሞን ለማ ከቤተሰባቸው ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ተገኝተው 4,000 የአሜሪካ ዶላር ድጋፍ አድርገዋል፡፡

በተመሳሳይ በግሬተር ፊለደልፊያ ነዋሪ የሆኑ ወገኖች የ3ሺህ አሜሪካን ዶላር ቦንድ በመግዛት በድምሩ 7,400 ዶላር መለገሳቸውን በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ፍጹም አረጋ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው አስታውቀዋል፡፡

ከተለያዩ ዳያስፖራዎች እስካሁን ከተሰበሰበው ግማሽ ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ወደ ሀገር ቤት መተላለፉን የገለጹት አምባሳደሩ፣ ለድጋፋቸውም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡