በደቡብና ጋምቤላ ክልል የፀጥታ ጉዳይ ውይይት

ነሐሴ 30/2013 (ዋልታ) በደቡብ እና ጋምቤላ ክልል አጎራባች ዞኖችና ወረዳዎች በሰላም፣ በልማትና በጸጥታ ጉዳዮች ላይ የጋራ የምክክር መድረክ በሚዛን አማን ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡
በመድረኩ የሁለቱ ክልሎች ርዕሳነ መስተዳድርና ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡
የደቡብ ክልል ምክትል ርዕስ መስተዳድር ርስቱ ይርዳው ሁለቱ ክልሎች በበርካታ ጉዳዮች መመሳሰል እንዳላቸው በመጥቀስ የጋራ እሴቶቻቸውን ለአብሮነትና ለሰላም መጠቀም ይገባል ብለዋል።
ክልሎቹ በተፈጥሮ ሃብት የበለፀጉ መሆናቸውን፣ የባህልና የቋንቋ መቀራረብን፣ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን መኖሪያ ቀጣና መሆናቸውንና ድንበር መጋራታቸው አንድ ያደርጉናል ያሉት ርስቱ ይህን እድል በመጠቀም የሁለቱን ክልል ነዋሪዎች ህይወት መቀየር አለመቻሉ የሚያስቆጭ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኡሞድ ኡጁሉ በበኩላቸው ሁለቱ ክልሎች በተፈጥሮ የተቸራቸውን የተፈጥሮ ሃብት ለዜጎች ለውጥና ዕድገት መጠቀም ሳይችሉ መቆየታቸውን አንስተው ይህን ችግር ለመቅረፍ በጋራ ለመስራት የሚመሩት ክልል ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
መረጃው የደሬቴድ ነው።