በጥቆማ የተያዘ 46 ሺሕ ሊትር ዘይት ለኅብረተሰቡ ሊከፋፈል ነው

መጋቢት 21/2014 (ዋልታ) በኅብረተሰቡ ጥቆማ በህገወጥ መንገድ በመኪና ተጭኖ የተያዘ ከ46 ሺሕ ሊትር በላይ ዘይት በመሰረታዊ ሸማች አማካኝነት ለኅብረተሰቡ ሊከፋፈል መሆኑ ተገለፀ።
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 አስተዳደር በመኪና ጥበቃ ላይ በተሰማሩ ነዋሪዎች ጥቆማ ከ2 ሺሕ 300 ካርቶን በላይ ዘይት ጭኖ የነበረ መኪና በኑሮ ውድነትና ገበያ ማረጋጋት ግብረ ኃይል ተወርሶ በወረዳው መሰረታዊ ሸማች ማኅበር አማካኝነት ለኅብረተሰቡ ሊከፋፈል መወሰኑን ወረዳው አስታውቋል።
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈፃሚ ትዝታ ነጋሽ ኅብረተሰቡ መሰል ህገወጥ ተግባራትን ሲመለከት ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ የተለመደ ትብብሩን እንዲቀጥል መጠየቃቸውን ከከንቲባ ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡