ኢትዮጵያና ብራዚል የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታወቁ

ግንቦት 14/2013 (ዋልታ) – የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ከብራዚል አቻቸው ጋር ሁለተኛውን የኢትዮ-ብራዚል የፖለቲካ የጋራ የምክክር መድረክ በዊቢናር አካሂደዋል።
ውይይቱ በሁለትዮሽ፣ ክልላዊና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ዙሪያ ስለሚደረጉ የጋራ ትብብሮች ላይ ያተኮረ ነበር።
በወቅቱም የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሶስትዮሽ ድርድር፣ በመጪው 6ኛው ብሔራዊ ምርጫ፣ በኢትዮ-ሱዳን የድንበር ጉዳይ እንዲሁም በትግራይ የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራትን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
አምባሳደር ሬድዋን ኢትዮጵያ ከብራዚል በተለያዩ መስኮች ትብብሮችን ለማጠናከር ያላትን ፍላጎት ገልጸዋል። ሀገራቱ በግብርና መሰረተልማት ዘርፎች ትብብሮችን ማጠናከር እንደሚያስፈልግም አንስተዋል።
አምባሳደር ኬኔት ዲኖሪንጋ ብራዚል በአፍሪካ አህጉር የምታደርገዉን ግንኘነት ለማሳደግ ከኢትዮጵያ ጋር በቅርበት መስራት ፍላጎት እንዳላቸዉ ገልጸዋል።
በዚህም ኢትዮጵያ በአህጉሩ ያላትን ሚና በመጠቀም ግንኝነቷን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ፍላጎት እንዳላት አስረድተዋል።
ሀገራቸው ዘመናዊ ግብርና እንዲሁም በአግሮ ፕሮሰሲንግ ዘርፍ በኢትዮጲያ ኢንቨስት ለማድረግ ዝግጅ መሆኗንም ገልጸዋል።
አያይዘውም በሀገራቱ መካከል ንግድና ኢንቨስትመንት ያለውን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር ሀገራቸው ፍላጎት ያላት መሆኑን አንስተዋል።
በፍትሕና ፀጥታ ዘርፎች በትብብር ለመሥራት እንዲሁም በባለብዙ ወገን መድረኮች ያላቸውን ትብብር ማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዩች ዙሪያ ምክክር ተደርጓል።
በቀጣይም በሁለቱ ሀገራት መካከል በተለያዩ ሴክተሮች ትብብሮችን የበለጠ ማጠናከር በሚቻልበት ዙሪያ ውይይት ተደርጓል።
ሁለቱ ሀገራት መካከል ለ70 ዓመታት የዘለቀ ዲፕሎማሲያዊ ግንኘነት እንዳላቸውም ተገልጿል።
(ምንጭ፡- የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባይ ጽሕፈት ቤት)