ኢትዮጵያና ፓኪስታን በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዘርፍ በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ምክክር ተደረገ

ሰኔ 22/2013 (ዋልታ) – ኢትዮጵያና ፓኪስታን በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዘርፍ በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ምክክር ተደረገ፡፡

በኢትዮጵያ የፓኪስታን አምባሳደር ሾዛብ አባስ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የስራ ኃላፊዎች ጋር ሁለቱ ሀገራት በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዘርፍ በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል።

አምባሳደሩ በአካባቢ ጥበቃ እና በውሃ ቴክኖሎጂ ዘርፍ ምርምር የሚያደርግና የእውቀት ሽግግር የሚፈጥር “የኢትዮ ፖኪስታን ሳይንቲፊክ ዲፕሎማሲ ፎረም” እንዲመሰረት ጠይቀዋል።

ፎረሙ በሳይንቲፊክ ጉዳዮች ዙሪያ ሁለቱ ሀገራት ያላቸውን ልምድ እንዲለዋወጡና በጋራ እንዲሰሩ የሚያስችል ነው ተብሏል።

ኢስላማባድ የሚገኘው COMSATS ዩኒቨርሲቲና የፓኪስታን ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርና ከሳይንስና ክፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጋር በጋራ የሚሰሩባቸው አሰራሮች በሚዘረጉበት ሁኔታ ላይም መክረዋል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) ፎረሙ እንዲመሰረት ድጋፋቸውን እንደሚያደርጉና ኢትዮጵያ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዘርፍ ያደረገቻቸውን የማሻሻያ ስራ ልምዶች ለፖኪስታን ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል።

የእስያ ሀገራት የዲጂታል እውቀት ላይ የተሻለ ልምድ ስላላቸው ኢትዮጵያም ከፓኪስታን ያሉ ልምዶችን ትወስዳለች ብለዋል።

በኢትዮጵያ የፓኪስታን አምባሳደር ሾዛብ አባስ በበኩላቸው፣ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ እየሰጡት ላለው ትክክለኛ መረጃ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ኃላፊዎች ምስጋና ማቅረባቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።