የሕወሓት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ የሰራዊቱን የድል ግስጋሴ አይገታም – መከላከያ ሰራዊት

ጥቅምት 16/2014 (ዋልታ) የሽብርተኛው ሕወሓት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ የሰራዊቱን የድል ግስጋሴ እንደማይገታው የአገር መከላከያ ሰራዊት አስታወቀ፡፡

የአገር መከላከያ ሰራዊት ባወጣው መግለጫ ሽብርተኛው ከሚታወቅባቸው ስልቶቹ መሀል አንዱ ቅጥፈቱ ነው ብሏል፡፡

ሙሉ መግለጫው ቀጥሎ ቀርቧል፡-

የሽብርተኛው የሀሰት ፕሮፖጋንዳ የሠራዊታችንን የድል ግስጋሴ አይገታውም !

ሽብርተኛው ከሚታወቅባቸው ስልቶቹ መሀል አንዱ ቅጥፈቱ ነው፡፡ ጉልበት ሲያንሰው ምላሱ ይረዝማል፤ ያልሆነውን ሆንኩ፣ ያላደረገውንም አደረኩ…ይላል፡፡ ይህ ደግሞ ጥርሱን የነቀለበት እና ተወልዶ ያረጀበት ባህሪው ነው፡፡

አንድም ቀን ከአፉ እውነት ተገኝታ የማታውቀው ይህ ሽብርተኛ፣ ሽንፈቱን የሚሸፍነው የሠራዊታችንን ስም በማጠልሸት ነው፡፡ ደጋፊዎቹ ኪሳራውን እንዳያወቁ ፣ ሰላማዊው ህዝብ ልጆቹን እና ምግብ እንዳይጠይቅ እንዲሁም አለም አቀፉ ማህበረሰብ ነውረኝነቱን እንዳይገነዘብ ሁል ጊዜ የተለመደች ስልት አለችው – የሠራዊታችንን ስም ማጠልሸት፡፡

ጀግናው ሠራዊታችን ባልዋለበት እና ባህሪው ባልሆነው ጉዳይ በጁንታው ፕሮፓጋንዲስቶች በስሙ ተደጋጋሚ ድራማ እየተሰራበት አይተናል፡ ሰምተናል፡፡ እዚህ ቦታ ሰላማዊ ህዝብ ገደል ከተተ፣ እዛ ደግሞ አቃጠለ… የሚሉ በውሸት ተቀነባብረው ለአለም የደረሱ ተውኔቶችን ታድመናል፡፡

እነዚህ በተደጋጋሚ በመከላከያ ሀይላችን ላይ ሲደረጉ የነበሩት የስም ማጥፋት ዘመቻዎች ልክ ጸሀይ እንደመታው የጠዋት ጤዛ ወዲያው እውነታው ታውቆ ይጋለጣሉ፡፡ ለጊዜው ደጋፊዎቹን ቢያስጨፍርም የኋላ ኋላ እውነቱን ህዝባችን እና አለም አቀፉ ማህበረሰብ እየተገነዘቡት መጥተዋል፡፡

መዋሸት የማይሰለቸው ይህ ቡድን አሁንም የሠራዊታችንን ስም ለማጥቆር በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ ሠራዊቱ ሰላማውያንን ገደለ፣ አረደ…የሚሉ ከብት ባልዋለበት አይነት ድራማ ለማሳየት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ ይህም እንደ ከዚህ ቀደሞቹ እርቃኑን መቅረቱ አይቀርም ፡፡ ምክንያቱም ቅጥፈትን የሚሸከም ህዝብ ስለሌለን፡፡

የመከላከያ ሠራዊታችን ሰብዓዊ ስሜት ያለው ህዝባዊነቱን ዛሬ ዛሬ አሸባሪው ህወሀት ቢክድም ዓለም የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡ ህዝብ ሲቸገር የሚያካፍል፣ ሲታመም የራሱን መድሀኒት የሚሰጥ ፣ ህዝብ ሲጠማ የሚያጠጣ፣ ሊገሉት የመጡት ሲማረኩ እንኳን የራሱን ሬሽን አካፍሎ ጦሙን የሚውል አዛኝ ፣  ሩህሩህ እና ደግ ሰራዊት ነው ያለን፡፡

የሠራዊታችን ባህሪ ይህ ሆኖ ሳለ የአሸባሪው ህወሀት ደጋፊዎች ሰሞኑን የተለመደ የፈጠራ ስራ እየፈበረኩ በማህበራዊ ሚዲያ ያሰራጩት የሠራዊቱን የደንብ ልብስ በመጠቀም በተደመሰሱት ታጣቂዎቹ ላይ የሚፈጽመው የተለመደ ድራማ መሆኑን ህዝባችን እንዲረዳ እየገለጽን ሠራዊታችን ወደፊትም የጀመረውን ሽብርተኞችን የማጽዳት ዘመቻ ከግብ ያደርሳል፡፡

ምንም እንኳን ጠላቶቹ ያልዋለበትን እና ባህሪው ያልሆነውን ጭቃ ሊለጥፉበት ቢሞክሩም፣ እሱ ግን እንደ እስካሁኑ ለእውነት እና ርትዕ በመቆም የድል ግስጋሴውን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡