የመዲናዋ ህንፃዎች ግራጫ ቀለም ሊቀቡ ነው በሚል የሚናፈሰው መረጃ ከዕውነት የራቀ ነው ተባለ

ዮናስ ዘውዴ

ግንቦት 13/2014 (ዋልታ) የአዲስ አበባ ህንፃዎች ሁሉ ግራጫ ቀለም ሊቀቡ ነው በሚል ከሰሞኑ በማኅበራዊ ትስስር ገጾች የሚናፈሰው መረጃ ከዕውነት የራቀ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ዮናስ ዘውዴ አስታወቁ።

የቢሮ ኃላፊው አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የህንፃ ስታንዳርድና የውጭ ማስታወቂያ ስታንዳርድ እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸው ሆኖም ግን ይህን መነሻ አድርጎ በማኅበራዊ ትስስር ገጾች አዲስ አበባ ከተማ ግራጫ ቀለም ልትቀባ ነው በሚል በስፋት ሲዘዋወር የታየው መረጃ የተሳሳተ ነው ብለዋል፡፡

እስካሁን ድረስ የከተማዋ ህንጻዎች ቀለም ምን አይነት ይሁን የሚለው ጉዳይ ለውይይት ቀረበ እንጂ የከተማ አስተዳደሩ በጉዳዩ ላይ ምንም አይነት ውሳኔ እንዳላሳለፈ አመልክተዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከዚህ ቀደም ‹‹ከተማችን ቡራቡሬ ሆና ባለቤት አልባ መስላለች›› ማለታቸውን ያስታወሱት የቢሮ ኃላፊው ይህን ችግር ማንኛውም የመዲናዋ ነዋሪ ሊታዘብ ይችላል፤ የከተማ አስተዳደሩም ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቷል ብለዋል።

ችግሩን ለመፍታት የውጭ ማስታወቂያውና የከተማዋ ቀለም ሁኔታ የሚመራበት ስታንዳርድ ዝግጅት ተደረገ እንጂ ውሳኔ ላይ አለመድረሱን ጠቁመዋል።

በቅርቡ በጉዳዩ ላይ ከባለሀብቶች ጋር ውይይት ተደርጎ እንደነበር ያስታወሱት ኃላፊው ይህን መነሻ አድርገው አንዳንድ ግለሰቦች ለግራጫ ቀለም የመሰላቸውን ትርጓሜ ሲሰጡ ተመልክተናል፤ ጉዳዩ በማኅበራዊ ትስስር ገጾች እንደሚዘዋወረው ተግባር ላይ የዋለ ሳይሆን ገና ለምክክር የቀረበ መሆኑን መገንዘብ ይገባል ብለዋል።

ከተማዋ ላይ አንድ አይነት ቀለም ብቻ ለቀለም ቅብ ሥራ ያስፈልጋል የሚል እሳቤ መያዝ እንደሌለበት የተናገሩት ኃላፊ ለአስፈላጊው ህንጻና አካባቢ የሚመጥን ዝብርቅርቅ ያልሆነና ለዓይን የሚማርኩ ቀለማትን የያዘ ስታንዳርድ እንደሚኖረን ይጠበቃል ማለታቸውን ኢፕድ ዘግቧል።