የብልጽግና ፓርቲ አንደኛ ጉባኤ የቅድመ ጉባኤ መድረክ ተጠናቀቀ

መጋቢት 1/2014 (ዋልታ) ለሶስት ቀናት በአዳማ ከተማ ሲካሄድ የነበረው የብልጽግና ፓርቲ አንደኛ ጉባዔ የቅድመ ጉባኤ መድረክ በዛሬው ዕለት ተጠናቋል፡፡

በማጠቃለያ መድረኩ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት ደመቀ መኮንን ከዚህ ቀደም በሀገራችን የሰራነውን የማፍረስ፣ አንድ ከሚያደርጉትን ይልቅ በሚያለያዩን ጉዳዮች ላይ ትኩረት ተደርቶ መስራት እንዲሁም ገቢራዊነት መጓደልና ግለሰቦች ከሀገር በላይ የሆኑበት ሁኔታዎች ይስተዋሉ ነበር ብለዋል፡፡

ብልጽግና እነዚህን ችግሮች በሚፈታ መልኩ እየተጓዘ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡

“ባለፉት ሶስት ዓመታት በበርካታ ተግዳሮቶች ውስጥም ሆነን የሀገራችንን ሉዓላዊነት በማስጠበቅ ስኬቶችን አስመዝግበናል ያሉት ምክትል ፕሬዝዳንቱ ፈተናውን በዘላቂነት ለመሻገርና ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ አንድነታችንን ማጠናከር አለብን” ብለዋል፡፡

የፓርው አመራርና አባላት በጥብቅ ስነ ምግባር መመራት አለባቸውም ብለዋል፡፡

በትስስርና እውቅና መስራት ብሎም ብልሹ አሰራሮች ለፓርቲው ጠንቅ መሆናቸውን ጠቅሰው ተግባሮችን ስንፈጽም በፓርቲው ህግና ደንብ እንዲሁም እሴቶችና መርሆዎች ተገዝተን መሆን አለበት ማለታቸውን የብልጽግና ፓርቲ መረጃ ያመላክታል።

ፓርቲው በቀጣይም ጥራት ላይ የተመሠረተ የአባላት ብዛት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አስታውቀዋል፡፡

የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አደም ፋራህ በበኩላቸው ከስርዓትና ከተልዕኮ አፈፃፀም-ጋር የሚያያዙ ችግሮችን መፍትሄ በመስጠት እንዲሁም ውስጣዊ አንድነትን በማጠናከር የፓርቲውን የአጭር ጊዜ እቅዶችና የረጅም ጊዜ ራዕይ ማሳካት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

አመራሩና መላ አባላቱ ጽንፈኛ ብሔርተኝነትን አምርረው እንዲታገሉም አሳስበዋል፡፡

ብልጽግና ፓርቲ አንደኛ ጉባኤውን ከነገ ጀምሮ ያካሂዳል።