የብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ጽህፈት ቤት የምርጡኝ ቅስቀሳ በአዲስ አበባ

መስከረም 9/2014 (ዋልታ) የብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ጽህፈት ቤት የምረጡኝ ቅስቀሳውን በአዲስ አበባ በማካሄድ ላይ ይገኛል።

በኢትዮጵያ 6ኛው ጠቅላላ ምርጫ በተካሄደበት ወቅት በሐረሪ ክልል አለመካሄዱ ይታወቃል።

የምርጫ ቦርድ 6ኛው አገራዊ ምርጫ ባልተካሄደባቸው አካባቢዎች መስከረም 20 ቀን 2014 ምርጫ ለማካሄድ በያዘው ቀጠሮ መሠረት በሐረሪ ክልል ምርጫው እንደሚካሄድ ተገልጿል።

በምርጫው የሚፎካከረው የብልጽግና ፓርቲም በምርጫው የህዝብን ድምጽ ለማግኘት በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ የምረጡኝ ቅስቀሳ እያካሄደ ይገኛል።

በመርኃግብሩም ላይ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲድ በድሪን ጨምሮ የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና በርካታ የክልሉ ተወላጆች እየተሳተፉ መሆናቸው ተገልጿል።

ከምርጫ ቅስቀሳው ጎን ለጎንም የደም ልገሣ መርሃ ግብር በመካሄድ ላይ ይገኛል።

በተያያዘም “የነጩ ፓስታ ጎርፍ ለነጩ ቤተ-መንግሥት” በሚል በአገር ደረጃ የተጀመረው ንቅናቄ በሐረሪ ክልል ደረጃ ዛሬ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በተገኙበት የሚካሄድ መሆኑም ተገልጿል።

የሐረሪ ክልል ምርጫ ከክልሉ ውጪ አዲስ አበባና ድሬዳዋን ጨምሮ ሌሎች በተመረጡ ቦታዎች የምርጫ ጣቢያ ተቋቁሞለት የሚካሄድ መሆኑን የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።