የአሜሪካ ኮንግረስ አባል ከኢትዮጵያ ጎን ልንቆም ይገባል አሉ

ታኅሣሥ 10/2014 (ዋልታ) የአሜሪካ ኮንግረስ አባል የሆኑት ሼይላ ጃክሰን ሊ ከኢትዮጵያ ጎን ልንቆምና ልንደግፋት ይገባል አሉ፡፡

ከከፋፋይ ኃይሎች በተቃራኒ ጎን ተሰልፈን የኢትዮጵያ መንግሥት ለሕዝቡና ለቀጣናው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚያደርገውን ጥረት መደገፍ አለብን ብለዋል።

የኢትዮጵያን የአግዋ ተጠቃሚነት ለማገድ የተላለፈው ውሳኔ ሊሰረዝና ኢትዮጵያ ወደ ስምምነቱ እንድትመለስ መደረግ እንዳለበት የምክር ቤት አባሏ አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡

የአሜሪካ ኮንግረስ አባሏ በቲውተር ገጻቸው ኢትዮጵያ በአፍሪካ ጠንካራ የምጣኔሃብት አንቀሳቃሽ ሞተር ነችም ብለዋል።

ኢትዮጵያ እንደ ዴሞክራሲያዊ እና ደኅንነቷ የተጠበቀ አገር ኅልውናዋ የተመሰረተው ለሕዝቧ በምታቀርበው የንግድ እና የምጣኔ ሃብት ዕድሎች ላይ እንደሆነም አክለዋል፡፡

በአፍሪካ ከቀረጥና ኮታ ነፃ የንግድ እድልን (አግዋ) ለመተግበር በተደረገው የመጀመሪያው የመክፈቻ ጉዞ ሼይላ ጃክሰን ሊ የልዑኩ አባል የነበሩ ሲሆን፤ አግዋ ከፀደቀበት ምክንያቶች አንዷ ኢትዮጵያ ነበረች ብለዋል።