የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ጄፍሬይ ፌልትማን በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት እያደረጉ ነው

ግንቦት 02/2013 (ዋልታ) የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ጄፍሬይ ፌልትማን በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት እያደረጉ ነው።

ከሚያዚያ 26 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በአፍሪካ የተለያዩ አገራት ጉብኝት እያደረጉ የሚገኙት ልዩ መልዕክተኛው ትናንት ኢትዮጵያ ገብተዋል።

ጄፍሬይ ፌልትማን ዛሬ ከውሃ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ ጋር በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታና የሶስትዮሽ ድርድር ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።

ለልዩ መልዕክተኛው በግድቡ ግንባታና የሶስትዮሽ ድርድር ዙሪያ በሚኒስትሩ ገለጻ ተደርጎላቸዋል።

ጄፍሬይ ፌልትማን ከኢትዮጵያ በፊት በግብጽ፣ በሱዳን እና ኤርትራ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በጉብኝታቸው ከአገራቱ መሪዎች ጋር በሁለትዮሽ ትብብርና ቀጠናዊ ጉዳዮች መምከራቸው የሚታወስ ነው።

ልዩ መልእክተኛው እስከ ግንቦት 5 ቀን 2013 ዓ.ም በአፍሪካ አገራት ከሚኖራቸው ቆይታ በተጨማሪ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅትና የአፍሪካ ህብረት የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ከፖለቲካ አመራሮችና ከሰብአዊ እርዳታ ተቋማት ሃላፊዎች ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የልዩ መልዕክተኛው ጉብኝት አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ በሚገኙ አገራት ያሉ የፖለቲካ፣ የጸጥታና ሰብአዊ ችግሮች በዲፕሎማሲያዊ ጥረት እንዲፈቱ ያላትን ቁርጠኝነት ማረጋገጥና በቀጠናው ያላትን የፖሊሲ ትብብር ማጠናከር አላማ ያደረገ መሆኑ መገለጹን ኢዜአ ዘግቧል።

ጄፍሬይ ፌልትማን በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ከሶስት ሳምንት ገደማ በፊት የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ሆነው መሾማቸው የሚታወስ ነው።

የ62 ዓመቱ ዲፕሎማት ከእ.አ.አ 1986 አንስቶ በተለያዩ አገራትና ዓለም አቀፍ ተቋማት በተለያዩ የስራ ሃላፊነቶች አሜሪካን ወክለው አገልግለዋል።