የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የጦር መሣሪያ አስተዳደርና ቁጥጥር መመሪያን አፅድቆ ወደ ስራ መግባቱን ገለፀ

ነሐሴ 4 ቀን 2014 (ዋልታ) የጦር መሣሪያ አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ ቁጥር 1177/2012 አንቀጽ 26 ንዑስ አንቀፅ 2 በሚደነግገው መሰረት አዋጁን ለማስፈፀም ይቻል ዘንድ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የጦር መሣሪያ አስተዳደር አጠቃቀም እና ቁጥጥር መመሪያ ቁጥር 02/2014 አጽድቆ ወደ ስራ መግባቱን ገለፀ።

ይህ መመሪያ የዳኝነት አካሉ የጦር መሣሪያ አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጁ ላይ ተመስርቶ ውሳኔ ለመስጠት ግልጽ እና ዝርዝር ጉዳዮችን ተመልክቶ በተቀራራቢና ተመሳሳይ የወንጀል ጉዳዮች መካከል ተቀራራቢነት ያለው ቅጣት እንዲወሰን ለማድረግ እንዲሁም እንደ ወንጀሉ ክብደትና አደገኛነት የቅጣት ተመጣጣኝነት ማረጋገጥን ግብ አድርጎ የወጣ ነው፡፡

በአዋጁ አንቀፅ 7 ንዑስ አንቀፅ 11 መሰረት የጦር መሳሪያ ፍቃድ የሚሰጥባቸው መስፈርቶችን በመመሪያው አንቀፅ 12፣ 15 እና 16 ተደንግጓል፡፡

በአዋጁ አንቀፅ 12 ንዑስ አንቀፅ 3 የጦር መሳሪያ ፍቃድ መስጫ መስፈርቶችን፣ ስለሚታደስበት ስርዓትና የጊዜ ገደብ በተመለከተ በመመሪያው አንቀፅ 33 ሥር ሰፍሯል፡፡

በአጠቃላይ በአዋጁ ላይ ግልጽ ያልሆኑ ጉዳዮችን በማያሻማ መልኩ እንዲቀመጡ የተደረገ ስለሆነ ለአዋጁ ተፈፃሚነት መመሪያው ጉልህ ድርሻ እንደሚያበረክት ይጠበቃል ተብሏል።

ስለሆነም የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ መመሪያው ከወጣበት ነሐሴ 04 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ሕገ-ወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውርን ለመግታት ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በተጠናከረ መልኩ እንደሚሰራ ገልጿል፡፡

በአዋጁ አንቀፅ 22 ንዑስ አንቀፅ 3 መሰረት ማንኛውም ሰው በህግ የተጣለውን ክልከላ እና ግዴታ በመተላለፍ የፀና ፍቃድ ሳይኖረው ብዛት ባለው የጦር መሣሪያ ወንጀል የፈፀመ እንደሆነ ቅጣቱ ከስምንት ዓመት እስከ ሃያ ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ከመቶ ሺሕ እስከ ሁለት መቶ ሺሕ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ እንደሚቀጣ አውቆ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አስታውቋል፡፡