ፌዴሬሽኑ የተመሠረተበትን 25ኛ ዓመት ክብረ በዓል እያከበረ ነው

ሚያዚያ 18/2014 (ዋልታ) የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኛ ማህበራት ፌዴሬሽን 25ኛ ዓመት የብር ኢዩቤልዩ ምስረታ በዓሉን “ጉዟችን ይቀጥላል” በሚል መሪቃል እያከበረ ይገኛል።

በአለማችን ከአንድ ቢሊዮን በላይ አካል ጉዳተኞች የሚገኙ ሲሆን በሃገራችን ኢትዮጵያም ወደ 20 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎቿ ከተለያየ ዓይነት የአካል ጉዳት ጋር እንደሚኖሩ መረጃዎች ያሳያሉ።

የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) አካል ጉዳተኞችን አስመልክቶ የወጡ ድንጋጌዎችን ከማስተዋወቅና የኅብረተሰቡን አመለካከት ለመለወጥ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ከዚህም ባሻገር ኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኛ ዜጎቿን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲሁም ማኅበራዊ ደኅንነታቸውን በማስጠበቅ ሁለንተናዊ ተሳትፏቸውንና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ጥረት እያደረገች እንደምትገኝ ተናግረዋል፡፡

በክብረ በዓሉ ላይ ሚንስትሮች፣ የመንግስት ከፍተኛ አመራሮችና የአካል ጉዳተኞች ማህበራት አመራሮች ተገኝተዋል።

በአሳንቲ ሐሰን