ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን 35 አባላት ያሉት የአማካሪ ኮሚቴ አቋቋመ

ግንቦት 9/2015 (ዋልታ) የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን 35 አባላትን ያቀፈ የአማካሪ ኮሚቴ ማቋቋሙን አስታወቀ።

ኮሚሽኑ ከኮሚቴው አባላት ጋር የትውውቅ መድረክ ያዘጋጀ ሲሆን በኮሚቴው እንዲካተቱ የተጋበዙ ግለሰቦች በተለያየ መልኩ ለኮሚሽኑ ስራዎች ድጋፍ የሚያደርጉ እንዲሁም በተለያየ ልምድ እና ሙያ ውስጥ መኖራቸውን ተገልጿል።

አባላቱ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ያሉ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ምሁራን እንዲሁም በምክክር ሂደት ላይ ስራዎችን ያከናወኑ ግለሰቦች እና የተቋማት ተወካዮች መሆናቸውም ተጠቁሟል።

ኮሚሽኑ ይህንን ኮሚቴ ሲያቋቋም በተቋቋመበት አዋጅ 1265/2014 ላይ ያሉ የህግ ማዕቀፎችን መሰረት በማድረግ መሆኑን ጠቅሶ ለኮሚቴው ስራዎችን የሚያከናውንበትን የውስጥ መመሪያ ማዘጋጀቱንም አስታውቋል።

የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ (ፕ/ር) በኮሚሽኑ የተከናወኑ ዋና ተግባራትን እና በቀጣይ ሊሰሩ የታቀዱ ስራዎችን በተመለከተ ለኮሚቴው አባላት ገለፃ ማድረጋቸውን ከኮሚሽኑ ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡