“ሃይማኖታችን ለሰላማችን” በሚል ሲካሔድ የቆየው ፀሎትና ምህላ መርሀግብር ተጠናቀቀ

ሚያዝያ 15 /2013 (ዋልታ) – ኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አስተባባሪነት ተዘጋጅቶ ለአንድ ሳምንት ሲካሄድ የቆየው ሀገራዊ የፀሎትና ምህላ የመዝጊያ መርሀግብር ተካሄደ፡፡

ለሀገር ሰላምና ደህንነት መጠበቅ እንዲሁም የኮሮና ወረርሽኝ ተፅዕኖ ሊያደርስ ከሚችለው የከፋ ጉዳት ፈጣሪ አትዮጵያን እንዲጠብቅ ሀገራዊ ፀሎትና ምህላ በሁሉም የሀይማኖት ተቋማት ሲካሄድ ቆይቷል።

“ሃይማኖታችን ለሰላማችን” በሚል ሲካሔድ የቆየው ፀሎትና ምህላ በኢትዮጵያ ማንነትን የለዩ ግድያዎችና መፈናቀሎች እንዲቆሙና የዜጎች መፈቃቀርን ፈጣሪ እንዲሰጥ ተማፅዕኖ የቀረበበት ነው፡፡

በአገሪቱ የሚታዩ ጥቃቶችና የሰላም እጦቶች እንዲሁም የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መበራከት ችግሮች ምክንያት የጸሎትና ምህላ መርሃ ግብር በሁሉም የሀይማኖት ተቋማት ሲካሄድ ቆይቷል፡፡

ሃይማኖታችን ለሰላማችን በሚል ሲካሔድ የቆየው ፀሎትና ምህላ በኢትዮጵያ ማንነትን የለዩ ግድያዎችና መፈናቀሎች እንዲቆሙና የዜጎች መፈቃቀርን ፈጣሪ እንዲሰጥ ተማፅዕኖ የቀረበበት ነው።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ፀሀፊ ሊቀትጉሀን ታጋይ ታደለ የሀይማኖት ተቋማት ለፍቅርና ሰላም የሚያደርጉትን ፀሎትና አስተምህሮ መንግስት ደግሞ ህግን በማስከበር ሊያግዝ ይገባል ብለዋል።

ለሀገር ሉዓላዊነት መጠበቅ እና ለሰላም መንግስት እና ህዝብ በቅድሚያ በመስጠት እንዲሰሩ ጉባኤው በመዝጊያ መርሀ ግብሩ ጥሪ አቅርቧል፡፡

በጸሎትና ምህላ መርሃ ግብሩ የኃይማኖት አባቶችም ምዕመናን የሰላም ተግባር መፈጸም እንዳለባቸው ማስተማር ይገባቸዋል ተብሏል፡፡

ሀገራዊው የጸሎትና ምህላ መርሃ ግብር ቢጠናቀቅም ምዕመናን በያሉበት የጸሎት ተግባራቸውን እንዲያደርጉ አባቶች መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በመርሀ ግብሩ የተገገኙት ዶ/ር ሊያ ታደሰ የሀገራዊውን ምህላ እና ጸሎት መርሀ ግብር እንዲከናወን ላደረጉ አካላት ምስጋና አቅርበው መርሀ ግብሩ ውጤት የሚያስገኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በአገር አቀፍ ደረጅ የጸሎትና ምህላ መርሃ ግብር በተቀመጠለት መርሀ ግብር እንዲካሄድ ትብብር ላደረጉ አካላት ምስጋናና የምስክር ወረቀት ተበርክቶላቸዋል፡፡
(በሰለሞን በየነ)