“ለበርካታ ዓመታት ንፁሃን ዜጎች በጅምላ በተገደሉበት ስፍራ የት/ቤት ግንባታ በማስጀመራችን ደስታ ይሰማናል” – ሙስጠፌ መሀመድ

ሚያዝያ 28/2014 (ዋልታ) “ለበርካታ ዓመታት የክልሉ ንፁሃን ዜጎች በጅምላ በተጨፈጨፉበት ስፍራ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ በማስጀመራቸው ከፍተኛ ደስታ ይሰማናል” ሲሉ የሶማሌ ከልል ርዕሠ መሥተዳደር ሙስጠፌ መሀመድ ተናገሩ፡፡
ርዕሠ መሥተዳድሩ ይህን ያሉት በቀብሪዳሀር ከተማ ለሚገነባው በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነ የ2ኛ ደረጃ ት/ቤት የመሠረት ድንጋይ ባሰቀመጡበት ወቅት ነው።
ትምህርት ቤቱ “ሰዎች ለሰዎች” በተባለው የጀርመን ዓለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅት ድጋፍ የሚገነባ መሆኑም ተገልጿል።
ርዕሠ መሥተዳደሩ የቀብሪዳሀር ከተማ እያደገች በመሆኗ የትምህርት አገልግሎትን በማጠናከር ጥራትና በቂ እውቀት ያለው ትውልድ መገንባት አስፈላጊ መሆኑን ገልፀዋል።
የቀብሪዳሀር ከተማ የሀገር ሽማግሌዎችም በበኩላቸው የክልሉ መንግሥት ከዚህ ቀደም በርካታ ንፁሃን ዜጎች በጅምላ ተገድለው በተቀበሩበት ስፍራ ለመታሰቢያነት የ2ኛ ደረጃ በማስገንባቱ ምስጋና ማቅረባቸውን ከሶማሌ ክልል ብዙሃን መገናኛ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡