ሚኒስቴሩ ለጅማ ዩኒቨርሲቲ የካንሰር ህክምና መስጫ ማዕከል ድጋፍ እንደሚያደርግ ገለጸ

መስከረም 30/2014 (ዋልታ) የጅማ ዩኒቨርሲቲን የካንሰር ህክምና ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥ ለማሟላት ለሚደረገው ጥረት መንግስት ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያደርግ የጤና ሚኒስትር ዲኤታ ዶክተር ደረጄ ዱጉማ ገለጹ።
ሚኒስትር ዲኤታው በ200 ሺህ ብር ወጪ የጨረር ህክምና መስጫ ማሽን የገባለትን የካንሰር ህክምና ማዕከል ትላንት ጎብኝተዋል፡፡
በዚህም ዶ/ር ደረጄ በኢትዮጵያ ውስጥ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በተለይ የካንሰር ስርጭት እየጨመረ ይገኛል ብለዋል።
የካንሰርን ህመም በመድኃኒት ለመፈወስ በርካታ ሙከራዎች መደረጋቸውን የገለጹት ዶክተር ደረጀ የጨረር ህክምናው የተሻለ ውጤታማ እንደሆነም ተናግረዋል።
“የአገልግሎቱ በጅማ መጀመር አዲስ አበባ ድረስ ሕክምናውን ለማግኘት ለሚቸገሩ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ለሚኖሩ ወገኖች ትልቅ ዕድል ነው” ብለዋል።
ሚኒስትር ዴኤታው በመሆኑም በጅማ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ማዕከል የጨረር ህክምና አገልግሎት መጀመሩ የሚደነቅ ነው” ሲሉ ገልጸዋል።
የህክምና ማዕከሉ በሙሉ አቅም መስራት እንዲችል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አስፈላጊውን የመሣሪያና የቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚያደርግም ዶክተር ደረጄ ቃል ገብተዋል።
በጅማ ዩኒቨርስቲ የሕክምና ማዕከል የኦንኮሎጂ ስፔሻሊስት ዶክተር አብዩ ለገሰ በበኩላቸው ማሽኑ ለካንሰር ህሙማን የህክምና አገልግሎት የጎላ መፍትሄ የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል።
በተጨማሪም ለታካሚዎች የተሻለ ሕክምና ለመስጠት የመጠባበቂያ ማሽን ፣ ማሽኑን ለማንቀሳቀስ ጄኔሬተርና ባለሞያዎችን መጨመር አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በጅማ ዩኒቨርሲቲ ጤና ኢኒስቲትዩት ሜዲካል ዶክተር አበበ ዱጉማ ከጨረር ህክምና በስተቀር የኬሞቴራፒ እና የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ይሰጥ እንደነበር ገልጸዋል፡፡
ለዚሁ የጨረር ህክምና የካንሰር ህመምተኞች ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተልከው ለ2 ዓመታት ያህል በቀጠሮ ሲጉላሉ ይቆዩ እንደነበር አውስተው ይህ ማሽን በጅማ ጤና ኢኒስቲትዩት ውስጥ መገኘቱ ለካንሰር ህመምተኞች ትልቅ ትርጉም አለው ብለዋል።
በአሁኑ ጊዜ የጨረር ህክምና ማሽኑ የሙከራ አገልግሎት እየሰጠ ሲሆን በቀን እስከ 10 ሕሙማንን እያገለገለ መሆኑን ገልጸው በሙሉ አቅሙ ሲሰራ ከዚህ የበለጠ አገልግሎት እንደሚሰጥ ማስረዳታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።