ምጣኔ ሃብቱ እንዳይዋዥቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኦሮሚያ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ አስታወቀ

ታኅሣሥ 16/2014 (ዋልታ) የአገርን ሉዓላዊነት ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ምጣኔ ሃብቱ እንዳይዋዥቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ አስታወቀ፡፡

የክልሉ የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ሀይሉ አዱኛ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ወረዳዎች ላይ የመስኖ ሥራ ተጠናክሮ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በ2013 ዓ.ም በሰብል ከተሸፈነ 5 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ውስጥ ከ4 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የተዘራ ሰብል መሰብሰቡን ጠቁመዋል።

በተያዘው የበጀት ዓመትም መጠነ ሰፊ የመስኖ ሥራዎችን በመስራት የአገሪቱ ኢኮኖሚ ሚዛኑን ጠብቆ እንዲጓዝ ማድረግ ይገባል ብለዋል።

ድርቅ በተከሰተባቸው የክልሉ አካባቢዎች ከ100 ሺሕ በላይ ኩንታል እህል ድጋፍ መደረጉንም አብራርተዋል።

ኃላፊው በክልሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከታወጀ በኋላ 1 ሺሕ 563 የአሸባሪው ሸኔ አባላት ላይ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል።