ሰብአዊ እርዳታ በጫነ ተሽከርካሪ ከ7 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ሕገወጥ ገንዘብ ተያዘ

ሐምሌ 29/2014 (ዋልታ) ሰብአዊ እርዳታ በጫነ ከባድ ተሽከርካሪ በሕገወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ ከ7 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ መያዙን በአፋር ክልል በጉምሩክ ኮሚሽን የሰመራ ቅርጫፍ ሰርዶ መቆጣጠሪያ ጣቢያ አስታወቀ።

የመቆጣጠሪያ ጣቢያው አስተባባሪ ኮማንደር አህመድ ሳልህ የእርዳታ እህል ሲጭኑ የነበሩ ከባድ ተሽከርካሪዎች  ከዚህ በፊት ነዳጅና ጨውን ጨምሮ የተለያዩ ህገወጥ እቃዎችን ለማሳለፍ ይሞክሩ ነበር ብለዋል።

ይህን ድርጊታቸው በፍተሻ ጣቢያው ሰራተኞች ጥብቅ ቁጥጥር ሲከሽፍ ፊታቸውን  ወደ ህገወጥ ብርና ልዩ ልዩ ጌጣጌጦችን የማዘዋወር ሥራ መግባታቸውን አብራርተዋል።

የመቆጣጠሪያ ጣቢያው ሰራተኞችና አመራሮች እየተለዋወጠ የመጣውን ህገወጥ ዝውውር  ለመቆጣጠር  በፈጠሩት መናበብ ተጨባጭ ውጤት እየታየ ለመሆኑ ሰሞኑ በጣቢያው የተያዙት ህገ ወጥ ብሮች በቂ ማሳያ ናቸው ብለዋል።

ዛሬም ከአዲስ አበበ ሰብአዊ እርዳታ ጭነው ይጓዙ የነበር ሁለት ተሽከርካሪዎች ላይ በተደረገ ፍተሻ ከ7 ሚሊዮን 900ሺሕ ብር በላይ በፍተሻ መያዙን ገልጸዋል።

ከዚህም ውስጥ የመጀመሪያው 2 ሚሊዮን 85 ሺሕ  200 ብር ዛሬ ጧት ሁለት ሰአት ኮድ3-64879 ኢ/ት ተሳቢ 25350 በሆነ ከባድ መኪና ላይ በጣቢያው ፈታሾች ገንዘቡ መያዙን አብራርተዋል።

በተጨማሪም  ኮድ3-12806 ኢ/ት ተሳቢ 06037 በሆን ተሽከርካሪ ከጧቱ 4 ሰአት በጣቢያው ሰራተኞች በተደረገ ፍተሻ 5ሚሊዮን 815 ሺሕ 400 ብር መያዙን ተናግረዋል።

ዛሬ የተያዘውን ጨምሮ በመቆጣጠሪያ ጣቢያ በአንድ ሳምንት ውስጥ ከ18 ሚሊዮን ብር በላይ ጥሬ ገንዘብ ሰብአዊ እርዳታ በጫኑ መኪኖች ላይ በተደረገ ፍተሻ መያዙን አስታውቀዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።