ሱዳን ኢትዮጵያ አንድ ሺህ ሜጋ ዋት ኃይል እንድትሸጥላት ጠየቀች

ሐምሌ 29/2013(ዋልታ) – ሱዳን አንድ ሺህ ሜጋዋት ኃይል ለመግዛት መጠየቋን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ገለጸ።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል የኮርፖሬት ፕላኒንግ ስራ አስፈፃሚ አቶ አንዱዓለም ሲዓ  እንደገለፁት፤ ሱዳንን ጨምሮ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ሃይል ለመግዛት ፍላጎት አሳይተዋል።

ቀደም ሲል ደቡብ ሱዳን፣ ኬንያ እና ጅቡቲ ከኢትዮጵያ ሃይል የመግዛት ፍላጎት አሳይተው ድርድር እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

በቅርቡ ሱዳን አንድ ሺህ ሜጋዋት ሃይል እንደምትፈልግ ማሳወቋን ጠቁሙ፤ ተቋማቸው ከሱዳን ባለሙያዎች ጋር እየተነጋገረ መሆኑን አቶ አንዱዓለም አስታውቀዋል።

ባለፈው ወር የተቋሙ ሠራተኞች ወደ ካርቱም አቅንተው እንደነበረና የሱዳን ባለሙያዎችም በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ውይይቱ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።

ለኬንያ የኤሌትሪክ ሃይል አቅርቦት 500 ኪሎ ዋት መሸከም የሚችል ማስተላለፊያ መስመር ዝርጋታ እየተጠናቀቀ መሆኑን የገለጹት አቶ አንዱዓለም፤ የኬንያ ፓርላማ ተወካዮች በቀጣዩ ሳምንት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በጉዳዩ ላይ ውይይት እንደሚያደርጉም አብራርተዋል።

ኢትዮጵያ ከኬንያ አልፎ ታንዛኒያ እስከ ደቡብ አፍሪካ ሁለት ሺ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፍ የሚያስችል መሠረተ ልማት መዘርጋቷንም ተናግረዋል።

ሶማሌላንድም ከኢትዮጵያ ሃይል ለማግኘት እንድትችል በዓለም ባንክ ድጋፍ ኢስት አፍሪካ ፖወር ፖሊሲ ከሚባል ተቋም ጋር ጥናት እየተደረገ መሆኑ አመልክትዋል።

ደቡብ ሱዳንም ሃይል እንዲቀርብላት በደብዳቤ ፍላጎቷን መግለጿን ጠቁመው፤ ይህን ተከትሎ የኤሌክትሪክ መስመር ዝርጋታ ማከናወን የሚያስችል ጥናት ለማድረግ የባለሙያዎች ቡድን በቅርቡ ወደ ደቡብ ሱዳን እንደሚያቀና ተናግረዋል።

እንደ አቶ አንዷለም ገለጻ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ትልቅ ፋይዳ አለው ።

አገሮቹ አሁን እያሳዩት ያለው የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎትም በግድቡ ያላቸውን ተስፋ እንደሚያመላክት መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል።