ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሲዳማ ቡና በአቻ ተለያየ

በ10ኛ ሳምንት ቤት ኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሲዳማ ቡና ያደረጉት ጨዋታ በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ፡፡

ረፋድ 4 ሰዓት ላይ በጅማ ዩኒቨርስቲ ስታድየም በተከናወነው ጨዋታ ሁለቱ ቡድኖች ተመጣጣኝ ፉክክር ቢያሳዩም ግብ ማስቆጠር አልቻሉም፡፡

በሙሉ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሲዳማ ቡና አራት የተሳካ የግብ ሙከራ ሲያደርግ ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ብቻ ነው ያደረገው፡፡

በሁለተኛው የጨዋታ አጋማሽ በሲዳማ ቡና በኩል ተከላካይ ፈቱዲን ጀማል በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል፡፡

ውጡቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከመሪው ፋሲል ከነማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ማጥበብ የሚችልበትን እድል አልተጠቀመም፡፡

የሊጉ 10ኛ ሳምንት ጨዋታ ዛሬ ሲቀጥል ቀን 9፡00 ሰዓት ላይ ሰበታ ከተማ ከሀድያ ሆሳዕና የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል፡፡

በአሸናፊ በቀለ የሚመራው ሀድያ ሆሳዕና በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ በ17 ነጥብ 2ኛ ላይ የተቀመጠ ሲሆን፣ ተጋጣሚው ሰበታ ከተማ ስድስት ነጥብ ብቻ በመያዝ ወራጅ ቀጠና ላይ ይገኛል፡፡

ለሁለቱም ቡድኖች የዛሬው ጨዋታ ውጤት ደረጃቸውን ለማሻሻል ወሳኝ ነው፡፡

ሊጉን ፋሲል ከነማ በ9ኝ ጨዋታ 22 ነጥብ በመያዝ ሲመራ፣ ሀድያ ሆሳዕና፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና እኩል 17 ነጥብ በመያዝ በግብ ክፍያ ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል፡፡

(በሀብታሙ ገደቤ)