በአዲስ አበባ ፖሊስ በሰራው የክትትል እና የቁጥጥር ስራ የተለያዩ ህገወጥ ተግባራት ማግኘቱን ገለጸ

ኅዳር 9/2014 (ዋልታ) በአዲስ አበባ ከተማ የሽብር ቡድኖቹን እኩይ አላማ ለማስፈጸም እና ለሰርጎ ገቦች ሽፋን ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ሲንቀሳቀሱ ፖሊስ ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት በተሰራው የክትትል እና የቁጥጥር ስራ የተገኙ ዋና ዋና ህገ ወጥ ተግባራት ያላቸውን እንደሚከተለው አስታውቋል፡፡

  1. በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የፀጥታ አካላት በህዝብ ጥቆማ መነሻነት ባደረጉት ክትትል በላስቲክ ቤት ውስጥ በርካታ ሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃዎች፣ ፓስፖርቶች፣ የተለያዩ ክልል የቀበሌ መታዎቂያዎች፣ ሌሎች ልዩ ልዩ ሰነዶችና ማህተሞች ተገኝተዋል፡፡
  2. ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 07 የረር በር ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የወረዳ 07 አስተዳደር ወሳኝ ኩነት ምዝገባ ሰራተኛ መኖሪያ ቤት ባደረገው ብርበራ የተለያዩ ንግድ ፈቃዶች፣ የትምህርት ማስረጃዎች፣ መሸኛ ደብዳቤዎች፣ የጋብቻ ማስረጃዎች እና ሌሎች ልዩ ልዩ ሰነዶች ተገኝተዋል፡፡ በተጨማሪ ማህተሞች እና ቲተሮች፣ ፍላሾች፣ ላፕቶፕ ኮምፒውተር እና ፎቶግራፍ የተለጠፈባቸውን ጨምሮ ለሃሰተኛ የነዋሪነት መታወቂያ መስሪያ የሚገለገልባቸው በርካታ ካርዶች እና ሃሰተኛ ሰነድ ሊዘጋጅባቸው የተሰጡ የበርካታ ግለሰቦች ፎቶ ግራፎች በብርበራ ተይዘዋል፡፡
  3. በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 ምስራቅ ሎቄ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ከህዝብ በደረሰው ጥቆማ በአንዲት ግለሰብ መኖሪያ ቤት ባደረገው ብርበራ መሬት ውስጥ ተቆፍረው በፌስታል ተጠቅልለው የተቀበሩ 2 ሽጉጥ ከ15 መሰል ጥይቶች ጋር፣ 70 ሺህ የኢትዮጵያ ብር፣ ሳንጃ እና የወርቅ እና የብር ጌጣጌጦች ከተደበቁበት ተቆፍረው እንዲወጡ ተደርጓል፡፡
  4. በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ልዩ ቦታው ሸራ ተራ የካቲት 23 ት/ቤት ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ አሸባሪዎቹን የህወሓትና የሸኔ ቡድኖች ሀገርን ለማፈራረስ እኩይ አላማ ማስፈፀሚያ ለማዋል 2 መቶ 76 ሲም ካርዶችና ሀሰተኛ የጦር መሳሪያ ፍቃዶች እንዲሁም የሽጉጥ ጥይቶች በህብረተሰቡ ጥቆማ በተከናወነው  የኦፕሬሽን ስራ በግለሰብ መኖሪያ ቤት በቁጥጥር ሥር ወለዋል፡፡
  5. በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 ወንድይራድ ትምህርት ቤት አካባቢ ህብረተሰቡ የሰጠውን ጥቆማ መነሻ በማድረግ ፖሊስ በአንድ ግለሰብ መኖሪያ ቤት ለብርበራ በሄደበት ወቅት 37 ሺሕ የአሜሪካ ዶላር፣ 52 ሺሕ ብር እና የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦችን በፌስታል ጠቅልሎ ግቢው ውስጥ ደብቆ ተገኝቶበታል፡፡

በተመሳሳይም 2ሺህ በላይ የክላሽን-ኮቭ ጥይት፣ 2 ክላሽንኮቭ ጠብመንጃ፣ 4 ሽጉጥ፣ 2 የጦር ሜዳ መነፅር፣ የእጅ መገናኛ ሬዲዮ ፣ ማህተሞችን እና ሲም ካርዶችን ህብረተሰቡ በሚሰጠው ጥቆማ በተደረገ  በብርበራ እና ፍተሻ መያዝ ተችሏል፡፡

  1. የመከላከያን ጨምሮ የፌዴራልና የክልል ፀጥታ ኃይሎች አልባሳት፣ ማዕረግና መለዮዎች፣ የጦር ሜዳ መነጽር፣ ኮምፓስ፣ ጂፒየስ፣ ተተኳሽ የቡድኑ መሳሪያ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ገንዘቦች ይገኙበታል። ለሽብር ተልዕኮ የሚያገለግሉ የሳተላይት ስልኮች፣ ሬዲዮ፣ ገመድ አልባ ስልኮች፣ ላፕቶፖች፤ የፎቶ ካሜራዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል። በፍተሻው ከተያዙ የጦር መሳሪያዎችና ተተኳሾች በተጨማሪ የተለያዩ ፈንጅና መሰል ነገሮችን በፌስታል እየተጠቀለሉ በጎዳና ላይ ተጥለው ተገኝተዋል፡፡

መረጃውን ያገኘነው ከአዲስ አበባ ከተማ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽ/ቤት ነው፡፡