አገራዊ አደራን ለመወጣት ህይወት እስከመስጠት ቁርጠኛ ውሳኔ

ነሐሴ 26/2013 (ዋልታ) – የተጣለብንን ሕዝባዊና አገራዊ አደራ በብቃት ለመወጣት ደም ከመለገስ ጀምሮ ህይወታችንን እስከመስጠት ድረስ ቁርጠኞች ነን ሲሉ የአፋር ክልል ምክር ቤት አባላት አስታወቁ።

የምክር ቤቱ አባላት ዛሬ ለመከላከያ ሰራዊትና ለሌሎች ጸጥታ ኃይሎች ደም ለግሰዋል።

የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባኤ አሚና ሴኮ በኃይል ሊጨፈልቀን የመጣውን ወራሪ አሳፍሮ በመመለስ ታሪካዊ ኃላፊነቱን መወጣት የሚቻለው ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል ከጸጥታ መዋቅሩ ጎን በመቆም በገንዘቡ ፣ ጉልበቱና እውቀቱ  የጀመረውን ደጀንነት  በማጠናከር እንደሆነ ገልጸዋል።

አሸባሪው የሕወሓት ቡድን በ”ጋሊኮማ ” የንጹሃን አርብቶ አደሮች ላይ የፈጸመውን የግፍ ጭፍጨፋ ያስታወሱት የምክር ቤቱ አባላት የጥፋት ቡድኑን  አገር የማፍረስ እኩይ ዓላማ ለማምከን የአፋር አርብቶ አደር ከሰራዊቱ ጎን በመሰለፍ  የህይወት ዋጋ እየከፈለ መሆኑን ተናግረዋል።