‘ኤችአር 6600’ እና ‘ኤስ 3199’ ረቂቅ ሕጎችን የሚቃወም ሰልፍ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው

መጋቢት 19/2014 (ዋልታ) ኢትዮጵያዊያንና ኤርትራዊያን የተሳተፉበት ‘ኤችአር 6600’ እና ‘ኤስ 3199’ ረቂቅ ሕጎችን የሚቃወም ሰላማዊ ሰልፍ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው።

በአሜሪካ መንግሥት መቀመጫ ‘ካፒቶል ሂል’ ፊት ለፊት እየተካሄደ በሚገኘው ሰልፍ ላይ ከአሜሪካ ከሚኖሩ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበረሰብ አባላትና ኤርትራዊያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች ተሳትፈዋል።

‘ኤችአር 6600’ እና ‘ኤስ 3199’ ረቂቅ ሕጎች የኢትዮጵያን ኅልውና የሚጎዳ እንዲሁም የኢትዮጵያና አሜሪካ ግንኙነት የሚያበላሽ በመኾኑ ሊሰረዝ ይገባል የሚል መልዕክት በሰልፈኞቹ እየተላለፈ ነው።

“ማዕቀብ መጣል ለኢትዮጵያ ጉዳትን እንጂ ምንም ጥቅም አያስገኝም ፤ ጎጂ የሆኑት ረቂቅ ሕጎች ውድቅ መደረግ አለባቸው” የሚሉ መፈክሮችም እየተላለፉ ነው።

በአሜሪካ የኮንግረስ አባል ቶም ማሊኖውስኪ (ኒውጀርሲ) ዋና አርቃቂነት፣ በያንግ ኪም (ካሊፎርኒያ)፣ ግሪጎሪ ሚክስ (ኒው ዮርክ)፣ ዴቪድ ሲሲሊን (ሮድ አይላንድስ)፣ ብራድ ሼርማን(ካሊፎርኒያ) እና ማይክል ማካውል (ቴክሳስ) ደጋፊነት የተዘጋጀው ‘ኢትዮጵያ ስታብላይዜሽን ፒስ ኤንድ ዴሞክራሲ አክት’ ወይም ኤችአር 6600 ረቂቅ ሕግ በኮንግረሱ የውጭ ጉዳዮች ኮሚቴ ውይይት እንደተደረገበት የሚታወስ ነው።

የ‘ኤችአር 6600’ ተጓዳኝ ወይም አጋዥ (ኮምፓኒየን ቢል) የሆነው የኢትዮጵያ ፒስ ኤንድ ዴሞክራሲ ፕሮሞሽን አክት ኦፍ 2021’ ወይም ‘ኤስ.3199’ በአሜሪካ ሴናተር ሮበርት ሜኔንዴዝ (ኒው ጀርዚ) ዋና አርቃቂነት፣ በሴናተር ጀምስ ሪስች (ኢዳሆ)፣ በሴናተር ክሪስ ኩንስ (ዴልዌር) እና በሴናተር ቶም ቲሊስ (ኖርዝ ካሮላይና) ደጋፊነት የተዘጋጀ ነው።

የአሜሪካ ሴኔት የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ በ‘ኤስ.3199’ ረቂቅ ሕግ ላይ ነገ ውይይት እንደሚያደርግ ኢዜአ በዘገባው አስታውሷል፡፡