ከንቲባ አዳነች የመንገድ ዳር የማስዋብ ሥራን አስጀመሩ

ግንቦት 25/2014 (ዋልታ) የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቂርቆስ ክ/ከተማ የሚገኘውን ከዑራኤል እስከ ፑሽኪን ያለውን መንገድ በአረንጓዴ የማስዋብ ሥራ አስጀምረዋል።
ፕሮጀክቱ በ60 ቀናት ከሚተገበሩ ሰው ተኮር ተግባራት መካከል አንዱ መሆኑን የተናገሩት ከንቲባ አዳነች አቤቤ እንደዚህ ዓይነት ተግባራት ከተማዋን በማስዋብና የዜጎችን አኗኗር በመቀየር ረገድ አስተዋጿቸው ከፍተኛ ነውና በሁሉም የከተማዋ አካባቢዎች በስፋት እየተሰሩ ነው ብለዋል።
ዜጎች በንፁህና አረንጓዴ ስፍራ የመኖር መብት እንዳላቸው የተናገሩት ከንቲባዋ የከተማ አስተዳደሩም የነዋሪዎቹን ፍላጎት ለማሟላት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው አዲስ አበባን እንደስሟ አዲስ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት መላው የከተማው ነዋሪዎች፣ ባለሃብቶችና በጎ ፍቃደኞች ከአስተዳደሩ ጎን በመቆም የበኩላቸውን አሻራ እንዲያስቀምጡ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።