ከኦፓል ማዕድን ሽያጭ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱ ተገለጸ

ኦፓል ማዕድን

ሐምሌ 14/2013 (ዋልታ) – በተጠናቀቀው 2013 በጀት ዓመት ለውጭ ገበያ ከተላከ የኦፓል ማዕድን ሽያጭ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የአማራ ክልል ማዕድን ማስፋፊያ ኤጀንሲ አስታወቀ።

የኤጀንሲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ይታየው ተስፋሁን በክልሉ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለማዕድን ሃብት ልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

በደቡብና ሰሜን ወሎ፣ በሰሜን ሸዋና ሌሎች አካባቢዎች የሚገኘውን የኦፓል ማዕድን የማውጣትና ወደ ገበያ የሚገባበትን መንገድ ሕጋዊ ለማድረግ እየተሠራ ነው ተብሏል፡፡

በተጠናቀቀው 2013 በጀት ዓመት ከ4 ሺህ 694 ኪሎ ግራም በላይ ጥሬ ኦፓልና ከ130 ኪሎ ግራም በላይ እሴት የተጨመረበት ኦፓል ወደ ህንድ፣ ቻይናና ሌሎች የእስያ ሃገራት ገበያ ተልኮ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ገቢ ተገኝቷል ብለዋል፡፡

በዘርፉ የተገኘው ገቢ ከ2012 በጀት አመት ጋር ሲነጻጸር በ1 ነጥብ 4 ሚሊየን ዶላር ብልጫ ማሳየቱን ኢዜአ ዘግቧል፡፡