የህዳሴ ግድቡ ከሀይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኛል

ነሐሴ 19/2014 (ዋልታ) ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከሀይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገቢ እንደሚያስገኝ ተገለጸ፡፡

የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ክፍሌ ሆሮ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሲጠናቀቅ የሚኖረውን አገራዊና ቀጣናዊ ፋይዳ አብራርተዋል።

የግድቡ ግንባታ ሙሉ ቡሙሉ ሲጠናቀ ከሀይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገቢ ያስገኛል ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከውሃ ብቻ እስከ 45 ሺሕ ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ ማመንጨት የምትችል መሆኑን ጠቁመው የጂኦ ተርማል፣ የፀሐይ እንዲሁም የነፋስ ኃይል ማመንጨት የሚያስችል እምቅ ሃብት አላት ብለዋል።

በመሆኑም ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብን ጨምሮ በሌሎችም የልማት መስኮች ለቀጣናዊ የልማት ትስስር ትኩረት ሰጥታ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ በሀይድሮ ኤሌክትሪክ ሀይል ከፍተኛ እምቅ ሀብት በመያዝ ከአፍሪካ ሁለተኛዋ ሀገር ብትሆንም፤ ከውሃ ሀብቷ የሚገባትን ጥቅም ሳታገኝ መቆየቷን አንስተዋል።

ግድቡ በሁለት ዓመት ተኩል እንዲጠናቀቅ እየሰራን ነው ያሉት ኢንጂነር ክፍሌ፤ በአሁኑ ወቅት ሁለት ተርባይኖች ኃይል ማመንጨት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል።

በቀጣይ ግንባታው ሙሉ ቡሉ ሲጠናቀቅ እና 11 ተርባይኖች ኃይል ማመንጨት ሲጀምሩ ኢትዮጵያ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ እንደምታገኝ ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ ያሏትን የውሃ ሀብትና ሌሎች የታዳሽ ኃይል እምቅ ሀብት በማልማት ለሀገራዊ እድገትና ለቀጣናው የኢኮኖሚ ትስስር መጠናከር እንደምትሰራም አብራርተዋል ያለው ኢዜአ ነው፡፡

ለዚህ ሀገራዊና ቀጣናዊ ሚና መሳካትና በህዳሴ ግድብ የተመዘገበው ድል በሌሎችም እንድቀጥል በትብብር መስራት አለብን ብለዋል።