የሉሲ ቅሪተ አካል መገኘት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የነበራቸው የስነ-ምድር ተመራማሪ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ

ነሀሴ 24 /2013 (ዋልታ) –የሉሲ ቅሪተ አካል መገኘት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የነበራቸው የስነ-ምድር ተመራማሪ ዶክተር ሞውራይስ ታይብ በ86 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ።
ሞውራይስ ታይብ የሉሲ ቅሪተ አካል በአፋር ክልል ሃዳር በተባለው አካባቢ መገኘት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደነበራቸው የፈረንሳዩ ብሔራዊ የሳይንስ ምርምር ማዕከል አስታውቋል፡፡
ዶክተር ሞውራይስ በአፋር ክልል የሃዳር አካባቢ በርካታ ጥንተ-ቅሪተ አካል ሊገኝበት እንደሚችል ቀደም ብለው ምርምር ካደረጉ ተመራማሪዎች መካካል አንዱ እንደነበሩም ተመላክቷል፡፡
ተመራማሪው የ3.2 ሚሊየን ዓመታት ዕድሜ ባለቤት የሆነችው የአውስትራሎ ፒተከስ አፋረንሲስ በልዩ መጠሪያ ስሟ ”ሉሲ ቅሪተ አካል” በስነ-ምህዳር ምርምር መገኘት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳበረከቱ ተነግሯል፡፡
ዶክተር ሞውራይስ ታይብ እኤአ በ1935 በቱኒዚያ የተወለዱ ሲሆን የዶክትሬት ትምህረታቸውን በእናታቸው ትውልድ ሀገር በሆነችው ፈረንሳይ በፓሪስ ስድተኛ ዩኒቨርሲቲ እኤአ በ1974 አግኝተዋል፡፡
ተመራማሪው እንደተመራቂ ተማሪ በአፋር አካባቢ የቅሪተ አካል ምርምር ማድረግ የሚያስችላቸውን ዓለም አቀፍ የአፋር የምርምር ማዕከል እኤአ በ1972 በማቋቋም ከሁለት ዓመታት በኋላ ከምርምር ባልደረቦቻቸው ዶናልድ ጆሃንሰን እና ይቨስ ኮፐንስ ጋር በመሆን በዓለም በሰው ዝግመተ-ለውጥ ጠቃሚ የሆነ ግኝት ማግኘታቸው ይነገራል፡፡
ዶክተር ሞውራይስ ታይብ እኤአ በ1996 የፈረንሳይ ብሄራዊ የሳይንስ ምርምር ማዕከል አካል በሆነው አይክስ ማርሴል ዩኒቨርሲቲ አባል በመሆን የስነ-ምድር፣ የአየር ንብረት ለውጥ ቅድመ ታሪክ ጥናት እና የአየር ንብረት ለውጥ ምክንያቶች ጥናት ትምህርት ክፍል አባል መሆን መቻላቸው እና በመቀጠልም የምርምር ማዕከሉ ዳይሬክተር ሆነው ማገልገላቸው ተዘግቧል፡፡