የመከላከያ ሰራዊት ቦንፎ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ የሸኔ ማሰልጠኛ ማውደሙ ተገለጸ

ግንቦት 30/2014 (ዋልታ) የመከላከያ ሰራዊት ቦንፎ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ የነበረውን የሸኔ ማሰልጠኛ ማውደሙ ተገለጸ።

ከሚያዝያ 17 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ሰራዊቱ ባከናወናቸው ተግባራት መተከል ዞን ድባጤ ወረዳ ቦንፎ የሚገኘውን የሸኔ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ያወደመ ሲሆን 43 የሸኔ አባላት ላይ እርምጃ መወሰዱና 60 አባላት በሰላም እጅ መስጠታቸው ተገልጿል።

በዚህም አሸባሪው ሲጠቀምባቸው የነበሩ 184 ኋላቀር መሳሪያዎች፣ 23 ክላሽንኮቭ፣ ከ300 ኩንታል በላይ በቆሎ፣ 16 ኩንታል አኩሪ አተር፣ ሁለት የፀሃይ ኃይል ማመንጫ (ሶላር)፣ ሁለት የእህል ሚዛን እና ሁለት ማዳበሪያ አደንዛዥ ዕፅ መያዙን ኮ/ል መኮንን ገጋዬ ገልፀዋል።

አሸባሪው ከኅብረተሰቡ ዘርፏቸው የነበሩ 47 የቀንድ ከብቶችና 60 ፍየሎችንም ማስመለስ መቻሉንም ተናግረዋል።

ለ3 ዓመታት በድባጤና በቡለን ወረዳዎች በሸኔና ፅንፈኛ ታጣቂዎች ስር የነበሩ 4 ቀበሌዎችም ነፃ መውጣታቸውም ተጠቁሟል።

በተገኘው አንፃራዊ ሰላም ተፈናቃዮችን ወደ አካባቢያቸው እየመለሱ እና ማኅበራዊ አገልግሎቱን በማስጀመር ላይ መሆናቸውን የድባጤ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ሙሉዓለም ዋወያ ገልጸዋል።

273 ታጣቂዎች በኮማንድ ፖስት ስልጠና ተሰጥቷቸው አካባቢያቸውን በመጠበቅ ላይ ይገኛሉ ማለታቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ያገኘነው መረጃ አመላክቷል።

ለፈጣን መረጃዎች፦
ፌስቡክ https://bit.ly/3Ma7QTW