የምሥራቅ ዕዝ የሰራዊት አባላት በአፋር ግንባር አሸባሪውን ሃይል በመደምሰስ አኩሪ ገድል እየፈፀሙ ነው – ሜጀር ጀነራል በላይ ስዩም

ነሃሴ 08/2013 (ዋልታ) – ህውሓት የተናጠል የተኩስ አቁሙን ባለመቀበሉ የመከላከያ ሠራዊቱ ከሌሎች የፀጥታ ሃይሎች ጋር በመተባበር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲደመስሰው አቅጣጫ መሰጠቱን የምሥራቅ ዕዝ ዋና አዛዥ ሜጀር ጀነራል በላይ ስዩም አስታውቀዋል ::
የምሥራቅ ዕዝ የሰራዊት አባላትም የተሰጣቸውን ትዕዛዝ መነሻ በማድረግ በተሰለፉበት የአፋር ግንባር አሸባሪውን ሃይል በመደምሰስ አኩሪ ገድል እየፈፀሙ መሆኑን የዕዙ ዋና አዛዥ ሜጀር ጀነራል በላይ ስዩም ገልጸዋል፡፡
አሸባሪው ቡድን ያሰለፋቸው አባላቱ ሰራዊቱ ባካሄደው የተቀናጀ የግዳጅ አፈጻጸም በርካቶች ሲደመሰሱ ቀሪው ደግሞ ቁስለኛና ምርኮኛ መሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡
ጠላት የጅቡቲን መስመር በመቁረጥ በሃገራችን ላይ ጉዳት ለመፈጸም አስቦ ቢንቀሳቀስም ምኞቱ በሰራዊቱ ቁርጠኝነትና አልበገር ባይነት አልተሳካለትም ብለዋል፡፡
በዕዙ ስር የሚገኙ የተለያዩ የሰራዊቱ አባላት በሰጡት አስተያየት ሰራዊቱ የአሸባሪውን ሃይል ለመደምሰስ ብቃቱም ሞራሉም እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች በሰጡት አስተያየት ተገደውና በሃሰት ፕሮፓጋንዳ ተታለው መግባታቸውን ገልጸዋል፡፡
ሜጀር ጀነራል በላይ ህዝቡ አሸባሪው ህውሓት ሆን ብሎ በሚያሰራጨው የሃሰት ፕሮፓጋንዳ መደናገር እንደሌለበትም አሳስበዋል፡፡