የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች የ3 ዓመት ልጄ ላይ መሳሪያ በመደገን አስገድደው ደፍረውኛል- የወልዲያ ከተማ ነዋሪ

ታኅሣሥ 11/2014 (ዋልታ) የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች የ3 ዓመት ልጄ ላይ መሳሪያ አቀባብለው በመደገን አስገድደው ደፍረውኛል ስትል የወልዲያ ከተማ ነዋሪዋ የግል ተበዳይ ገለጹ፡፡

የወልዲያ ከተማ ከአሸባሪው ሕወሓት ቡድን ነፃ መውጣቷን ተከትሎ ወራሪው ቡድን በከተማዋ በቆየባቸው ጊዜያት ውስጥ የፈፀማቸው ለመስማት የሚከብዱ ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና የንብረት ውድመቶች ገሃድ እየወጡ ነው።

አሸባሪውና ወራሪው ቡድን በወልድያ ከተማ በቆየባቸው ጊዜያት ንጹሐንን በአደባባይ ረሽኗል፣ የመንግስት ተቋማትና የግለሰብ ሀብት ዘርፏል እንዲሁም ሴቶችን አስገድዶ ደፍሯል።

የሽብር ቡድኑ ሰይጣናዊ ተግባር የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ሰለባ መሆኗን ተናግራለች፡፡

ወጣቷ ለኢዜአ እንደተናገረችው “ነሐሴ 7 ቀን 2014 ምሽት ላይ ዝናብ እየዘነበ ነበር፣ በቁጥር በርከት ብለው ወደ ቤት መጡ፣ ዝናቡን ለማሳለፍ እንደሆነ ነገሩኝ፣ ከደቂቃ በኋላ ቤት መግባት እንደሚፈልጉ ሲነግሩኝ አልከፍትም አልኳቸው፣ ቆይተው የተደበቀ ወታደር ካለ ልናይ ነው ክፈችው እያሉ በሩን በኃይል መደብደብ ጀመሩ።”

ባለቤቷን ከአንድ ዓመት በፊት በሞት እንዳጣችና ከሶስት ዓመት ልጇ ጋር እንደምትኖር ብትነግራቸውም መስማት አልፈለጉም። በሩን ሰብረው በመግባት ያለውን ነገር ከፈተሹ በኋላ ሰው ሲያጡ የሶስት ዓመት ህጻን ልጄ ጭንቅላት ላይ መሳሪያ አቀባብለው አስገድደው ደፈሩኝ ብላለች።

በወቅቱ ከኔ ጋር ለማደር የመጣችን የ14 ዓመት ልጅ ከተዘጋ የጎረቤት ቤት በመውሰድ ለአራት ደፍረዋታል ብላለች።

ህፃኑ ልጅ በወቅቱ የነበረው ሰቆቃ አልረሳ ብሎት ሌሊት ይቃዣል፣ መሳሪያ የያዘ ሰው ሲያይ በድንጋጤ እያለቀሰ የስነልቦና ጫና ተፈጥሮበታልም ነው ያለችው።