የኢትዮጵያ ጦርነት ከአሜሪካ ጋር ነው- የካናዳ ዓለም ዐቀፍ የወንጀል ሕግ ባለሙያ

ታኅሣሥ 28/2014 (ዋልታ) በኢትዮጵያ ያለው ጦርነት የእርስ በርስ ጦርነት ሳይሆን የተላላኪውና አሸባሪው ትሕነግ አጋር በሆነችው አሜሪካና በኢትዮጵያ መካከል የተደረገ ነው ሲሉ የካናዳ ዓለም ዐቀፍ የወንጀል ሕግ ባለሙያው ጆን ፊልፖት ገለፁ።

የሕግ ባለሙያው አንዳንድ የአውሮፓ እና የአሜሪካ ዲፕሎማቶች ለአሸባሪው ትሕነግ ሲያደሉ ማስተዋላቸውን ለኢዜአ ተናግረዋል።

የውክልና ጦርነቱ በኢትዮጵያ ላይ የሚደረግ ወረራና የጥቃት ዓይነት መሆኑን አንስተዋል፡፡

ድርጊቱ በተለያዩ አገራት መፈጠሩንም ጠቅሰው በዓለም ዐቀፍ ሕጎች በሚቀጥሉት 10 እና 20 ዓመታት ውስጥ መፍትሄ የሚያገኝ ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ በራሷ ወሰኗንና ድንበሯን ማስጠበቅ ትችላለች በዚህም ለአፍሪካ ሁሉ አንጸባራቂ ብርሃን የመሆን ትልቅ አቅም አላት ሲሉም ገልጸዋል፡፡

አገሪቱ ወደ ሰላም እየተመለሰች ባለችበት፣ በርካታ ዲያስፖራዎች ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ባለበት በአሁኑ ወቅት የአሜሪካ ኤምባሲ ሰሚ ያጣበትን ከኢትዮጵያ ውጡ የሚል ልመና ዛሬም በመግለጫ ማውጣቱ በእርግጥም የካናዳው የሕግ ባለሙያ እንደሚሉት ጦርነቱ ከአሜሪካ ጋርም ጭምር ለመሆኑ አንዱ ማሳያ ሆኖ ይወሰዳል፡፡