ዱባይ 2020 ኤክስፖ ከጥቅምት 1 ይጀምራል


ነሀሴ 4/2013 (ዋልታ) –
በኮቪድ ተራዝሞ የነበረው ዱባይ 2020 ኤክስፖ በፈረንጆቹ ጥቅምት 1 እንደሚጀምር ተገለጸ፡፡
ኤክስፖው ኢትዮጵያን በተለያየ መልኩ ለማስተዋወቅ ሰፊ እድል ይፈጥራል ተብሏል፡፡
በኤክስፖው ላይ ኢትዮጵያን የሚገልጹ ሙዚቃዎች፤ ባህሎች እና የተለያዩ ሀገሪቱን የሚያስታውሱ ቀኖች ተሰይመው ይከበራሉ ተብሏል፡፡
የቡና፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንት፣የብሄራዊ ክብረ-በዓል ቀናቶች እንደሚከበሩ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የወጪ ንግድ ማስፋፊያ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ ገልጸዋል፡፡
ኤክስፖው በፈረንጆቹ ከጥቅምት 01 ቀን 2020 እስከሚያዝያ 20 ቀን 2021 ሊካሄድ የነበረ ቢሆንም በኮቪድ-19 ዓለማቀፍ በወረርሺኝ ምክንያት በፈረንጆቹ ከጥቅምት 1 ቀን 2021 እስከ ሚያዝያ 31 ቀን 2022 ይካሄዳል፡፡
በኤክስፖው ከተሳትፎ የቀረቡት ሶስት ንዑስ ክፍሎች መካከል ዕድል፣ ተንቀሳቃሽነት እና ዘላቂነት የሚሉ ይገኙበታል፡፡
ባህልና ቅርሶችን፤ ኢንቨስትመንትን፣ ንግድና ቱሪዝምን በማስተዋወቅ ከፍተኛ ሚና የምኖረው የኤክስፖው ንዑስ ክፍል ዕድል በመሆኑ ሀገራችንም የምትሳተፍበት የኤክስፖው ንዑስ ክፍል መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ Land of origins & opportunities በሚል መሪ ቃል በመሳተፍ በዋናነት ዳያስፖራውን፣ የግሉን ዘርፍ፣ እንዲሁም ክልሎችን እና የባህል አምባሳደሮችን በማካተት የኢትዮጵያን ኢንቨስትመንት፣ ንግድና ቱሪዝም ለማስተዋወቅ እየተሰራ ነው ማለታቸውን ከንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡