ጂግጅጋ ዩኒቨርሲቲ በደሴ ከተማ ለተጠለሉ ተፈናቃዮች ድጋፍ አደረገ

ነሃሴ 14/2013 (ዋልታ) – የጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ በአሸባሪው ህወሓት ተፈናቅለው በደሴ ከተማ ለተጠለሉ ወገኖች ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የምግብ እህልና የቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ።

የዩኒቨርሲቲው ተወካይ ዶክተር ዑመር ኑሩ በአሸባሪው ህወሓት ከሰሜን ወሎ ዞን ተፈናቅለው በደሴ ከተማ ለተጠለሉ ተፈናቃዮች የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አጋርነቱን አሳይቷል ብዋል።

“ወሎ ዩኒቨርሲቲ ባደረገልን ጥሪ መሰረት የጀመርነውን ድጋፍ አጠናክረን እንቀጥላለን” ያሉት ዶክተር ዑመር፤ 200 ብርድ ልብስ፣ 150 ፍራሽ፣ 200 ጥንድ አንሶላ፣ 70 ካርቶን ፓስታ፣ ባለ 25 ሊትር 100 ጀሪካን ዘይት፣ ከ30 ኩንታል በላይ ሩዝና ማካሮኒ ድጋፍ ማድረጋቸውን ነው የገለፁት፡፡

የወሎ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዶክተር አፀደ ተፈራ በበኩላቸው “ወቅቱ ዩኒቨርሲቲዎች የማህበረሰብ አገልግሎት በመስጠት የህዝብ አጋርነታቸውን በተግባር የሚያሳዩበት ነው” ብለዋል፡፡

የተፈናቃዮች ቁጥር በየቀኑ እየጨመረ በመምጣቱ ሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ድጋፍ በማድረግ አጋርነታቸውን እንዲያሳዩም ጥሪ አቅርበዋል።

የደሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰይድ እሸቱ መንግስት ህብረተሰቡንና ተቋማትን በማስባበር የእለት ደራሽ ምግብ ለማቅረብ ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

በደሴ ከተማ በስምንት ትምህርት ቤቶች ተጠልለው ከሚገኙት ከ60 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች በተጨማሪ በዘመድ ቤት፣ በኪራይ ቤትና በሌሎችም ስፍራዎች እጅግ ብዙ ተፈናቃዮች እንደሚገኙ ኤዜአ ዘግቧል፡፡