ጃፓን ለትግራይ ክልል የ265 ሚሊየን ብር ድጋፍ ይፋ አደረገች

የካቲት 10/2013 (ዋልታ) – ጃፓን በትግራይ ክልል በተካሄደው የህግ ማስከበር ዘመቻ ጉዳት ለደረሰባቸው እና ለተፈናቀሉ ወገኖች የሚውል ድጋፍ ይፋ አደረገች፡፡

ድጋፉ በአብዛኛው ሴቶችና ህጻናትን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑንም የጃፓን ኤምባሲ አስታውቋል፡፡

አጠቃላይ ድጋፉ 265 ሚሊየን ብር ሲሆን፥ የምግብ፣ መጠለያ፣ የንጽህና መጠበቂያ፣ አልሚ ምግቦች እና ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁሶችን ያካተተ ነው፡፡

ድጋፉ በዓለም የምግብ ፕሮግራም፣ በዓለም አቀፉ የፍልሰተኞች ድርጅት፣ በዩኒሴፍ፣ በተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር፣ በተመድ የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ፅህፈት ቤት እና በዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ አማካኝነት ለተጎጂዎች የሚዳረስ ይሆናል፡፡

ኤምባሲው የጃፓን መንግስት በትግራይ ክልል ያለውን ሁኔታ ለማሻሻል በትብብር መስራቱን እንደሚቀጥልም ገልጿል፡፡