ፈረንሳይ ለኢትዮጵያ ድጋፍ እንደምታደርግ አስታወቀች

ጥር 24/2014 (ዋልታ) ፈረንሳይ ኢትዮጵያን በመልሶ ግንባታና ሊደረግ በታሰበው አገራዊ የምክክር መድረክ ረገድ ከፍ ያለ ድጋፍ እንደምታደርግ አስታወቀች፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በአፍሪካ ቀንድ ከፈረንሳይ ልዩ መልዕክተኛ አምባሳደር ፍሬድሪክ ክላቬር ጋር ተወያይተዋል፡፡
በውይይታቸውም የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ፣ ቀጣናዊና የሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያና ፈረንሳይን ዘመን የተሻገረ ግንኙነት አድንቀው በኢትዮጵያ በኩል የግንኙነቱን መሰረቶች ይበልጥ ለማጠንከር ፍላጎት እንዳለ አስረድተዋል፡፡
መንግሥት ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ እየወሰዳቸው ያላቸውን እርምጃዎች ያነሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወሳኝ ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ስለሚወያየው አገራዊ የምክክር መድረክም አብራርተዋል፡፡
በፖለቲካው መድረክ ከፍ ያለ ስም ያላቸው ሰዎች ከእስር መፈታትም ለምክክሩ ስኬት አበርክቶ እንደሚኖረው መናገራቸውንም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ይጠቁማል፡፡
በሌላ በኩል ለሰላም ባለው ፍላጎት መንግሥት ወታደሮቹን ወደ ትግራይ ክልል እንዳይገቡ ቢያደርግም አሸባሪው ትሕነግ በጎረቤት ክልሎች የጀመረው አዲስ ጥቃት የተጠበቀውን ውጤት የሚቀለብስ እንዳይሆን ያሰጋል ሲሉም አክለዋል፡፡
.
ልዩ መልዕክተኛው በበኩላቸው አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከር ፍላጎት እንዳላት አንስተው በመልሶ ግንባታና ዘላቂ ሰላምን እንደሚያመጣ ተስፋ በተሰነቀበት ሁሉን አካታች አገራዊ የምክክር መድረክ ረገድ ፈረንሳይ ንቁና ከፍ ያለ ድጋፍ እንደምታደርግ ገልጸዋል፡፡