ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የመፈጸም አቅም ማደግ እንዳለበት ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል አሳሰቡ

ግንቦት 27/2014 (ዋልታ) የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል ከፋለ (ዶ/ር) በክልሉ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የመፈጸም አቅምን በማሳደግ የሕዝብ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እንደሚገባ አሳስበዋል።

ርዕሰ መስተዳድሩ በደቡብ ጎንደር ዞን የሚገኘውን የታችኛው ርብ መስኖ ልማት ፕሮጀክት የሥራ አፈጻጸም ተመልክተዋል። በመስክ ምልከታው ላይ የተለያዩ የክልልና የዞኑ የሥራ ኀላፊዎች ተገኝተዋል።

የታችኛው ርብ መስኖ ልማት ፕሮጀክት የመጀመሪያ ዙር ግንባታው ሲጠናቀቅ 3 ሺሕ 100 ሄክታር መሬት በመስኖ ለማልማት እንደሚያስችል ተገልጿል።

አሁን ላይ ቀሪ ሥራዎችን በ16 ወራት አጠናቆ ለማስረከብ ውል ወስዶ የሚሠራው ሀገር በቀሉ ዓባይ ኮንስትራክሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ነው። ሥራውን የካቲት 2013 ዓ.ም የጀመረ ሲሆን ሰኔ 30/2014 ዓ.ም የማስረከቢያ ጊዜ እንዲሆን ውል ተወስዷል።

ይሁንጅ አሁናዊ የሥራ አፈጻጸሙ ገና 21 በመቶ ላይ እንደሚገኝ የሳይት ተቆጣጣሪው ኢንጅነር ታገሰ ዓለማየሁ ተናግረዋል።

እንደ ኢንጅነር ታገሰ ገለጻ ለፕሮጀክቱ መዘግየት ምክንያት የመጀመሪያው ካሳ የተከፈላቸው አርሶ አደሮች በጊዜ አለመነሳት ነው ብለዋል። ውል ወስዶ ግንባታውን የሚሠራው ተቋራጭ አቅም ውስንነትም የመዘግየቱ አንዱ ምክንያት እንደሆነ ጠቅሰዋል።

ችግሩን ያዩት የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል ከፋለ (ዶ/ር) የመስኖ ፕሮጀክቱ ችግሮች ተፈተው በቀጣይ ዓመት ወደ ሥራ እንደሚገባ ተናግረዋል።

የርብ መስኖ ፕሮጀክትን ጨምሮ ሌሎችንም ፕሮጀክቶች በጊዜ በማጠናቀቅ የአማራ ክልልን የመስኖ ልማት ሽፋን ለማሳደግ የክልሉ መንግሥት በልዩ ትኩረት እየሠራ እንደሚገኝም ተናግረዋል።

ከመስኖ ግድቦች በተጨማሪም አነስተኛ የወንዝ ውኃ መጥለፊያ የፓንፕ ጀነሬተሮችን በመግዛት ለአርሶ አደሩ ለማሰራጨት የክልሉ መንግሥት እቅድ መያዙን ገልጸዋል ሲል አሚኮ ዘግቧል።

ርዕሰ መስተዳድሩ በአማራ ክልል የሚከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ውስጥ የማጠናቀቅ አቅምን በማሳደግ የሕዝብ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እንደሚገባም አሳስበዋል።