የውጭ ምንዛሪ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል የአሠራር ሥርዓት በቅርቡ ይፋ ይደረጋል

የውጭ ምንዛሪ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል አዲስ የአሠራር ሥርዓት ጥናት  መጠናቀቁንና  በቅርቡ  ለህዝብ  ይፋ  ተደርጎ  ወደ ሥራ  እንደሚገባ  የብሔራዊ ባንክ አስታወቀ ።

የብሔራዊ ባንክ ዋና ገዥ ዶክተር  ይናገር  ደሴ የውጭ  ምንዛሪን  በተመለከተ  ከተለያዩ የባለድርሻ አካላት ባደረጉት ውይይት እንደገለጹት አገሪቱ ያጋጠማትን የውጭ ምንዛሪ እጥረት  ለመፍታት  መንግሥት  የተለያዩ  ስልቶችን  ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ።

ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ ያቀረቡትን ጥሪ ተከትሎም በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ገንዘቦች ወደ ባንክ እየመጣ ስለመሆኑም የተናገሩት ዶክተር ይናገር በቅርቡ ዝርዝር መረጃው ለህብረተሰቡ ይፋ ይደረጋል  ብለዋል ።

በአገር ውስጥ ባለሃብቶችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ከውጭ ምንዛሪ ጋር በተያያዙ የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት ከመንግሥት ተባብረው እንዲሠሩም ዶክተር ይናገር ጥሪ አስተላልፈዋል ።

ዶክተር ይናገር ከባለድርሻ አካላት ጋር ባደረጉት ውይይትም ከባለሃብቶች ለቀረቡላቸው ቅሬታዎች በሠጡት ምላሽ እንደገለጹት በቅርቡ በአገሪቱ ለውጭ ምንዛሪ እጥረት መከሰት የውጭ ምንዛሪ  አፈጻጸም  ዝቅተኛ መሆን በምክንያትነት ይጠቀሳል ብለዋል ።

በተጨማሪም ወቅቱ የሚጠይቀውን መስፈርት ያላሟሉ መመሪያዎችና አሠራሮች እንዲሁም ኃላፊነት የጎደላቸውና ለግል ጥቅማቸው ቅድሚያ የሠጡ የብሄራዊ ባንክ አመራሮችና ሰራተኞች ለተፈጠረው ችግር የራሳቸውን አስተዋጽኦ  ማበረከታቸውን ገልጸዋል ፡፡