የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ከንብረት ዘረፋ ጋር በተገናኘ እየተወዛገቡ ነው

የሰማያዊ  ፓርቲ አመራሮች ከንብረት ዘረፋ ጋር  በተገናኘ  ውዝግብ  ውስጥ  መግባታቸውን ተገለጸ

የሰማያዊ ፓርቲ ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን የፓርቲውን ሊቀመንበር አቶ ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር) እስከ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ ፓርቲውን ወክለው ምንም ዓይነት ሥራም ሆነ እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ፣ ከመስከረም 20 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ማገዱን አስታወቀ፡፡

የፓርቲው ማኅተም መጥፋቱና ከመስከረም 19 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በማኅተሙ የሚሠራጭ ማንኛውም ደብዳቤ ሕገወጥ መሆኑ ለሕዝብና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ይፋ ከተደረገ በኋላ፣ ኮሚሽኑ ማኅተሙን ተጠቅሞ የዕግድ ደብዳቤ ማውጣት ካለመቻሉም በተጨማሪ እሳቸውን የማገድ ሥልጣን እንደሌለው አቶ ይልቃል ተናግረዋል፡፡

የፓርቲው ኦዲት ምርመራና ኮሚሽን ‹‹ሕዝብ የማወቅ መብት አለው›› በሚል ርዕስ ባወጣው ደብዳቤ እንደገለጸው፣ የፓርቲው ሥነ ሥርዓት ኮሚቴ ከመጋቢት 11 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በእነ አቶ ይልቃል ጌትነት ላይ በቀረበው ቅሬታ ላይ ውሳኔ አስተላልፎ ነበር፡፡

 ነገር ግን የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽኑ ኮሚቴው ያስተላለፈውን ውሳኔ በማገድ ሲመረምር ከርሞ፣ ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ዕግዱን አንስቷል፡፡ እነ አቶ ይልቃልም በ15 ቀናት ውስጥ ይግባኝ እንዲሉ ጊዜ መስጠቱን ጠቁሟል፡፡

እነ አቶ ይልቃል የይግባኝ ጊዜያቸውን ሊጠቀሙበት ባለመቻላቸው፣ የኮሚቴውን ውሳኔ ማፅናቱን የገለጸው ኮሚሽኑ፣ አቶ ይልቃል ጠቅላላ ጉባዔው እስከሚደረግበት መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ ፓርቲውን በሕጋዊ ሰውነት መወከልም ሆነ ሥራ መሥራት እንደማይችሉ አስታውቋል፡፡

የፓርቲው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን የፓርቲውን ሊቀመንበር ማገዱን በሚመለከት ጥያቄ የቀበላቸው አቶ ይልቃል ጌትነትን በሠጡት ምላሽ ፣ ‹‹ኮሚሽኑ የማገድ ሥልጣን የለውም፡፡ ሊቀመንበሩን የመረጠው ጠቅላላ ጉባዔ ስለሆነ፣ ማገድም ሆነ የሚሽረው ጠቅላላ ጉባዔ ነው፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ይልቃል የሰማያዊ ፓርቲ ከቀናት በፊት ማኅተሙን ጨምሮ በርካታ ንብረቶቹ በመዘረፋቸው፣ ለሚመለከተው የመንግሥት ተቋም ማሳወቃቸውንና ኃላፊዎችን በሕግ ለመጠየቅ በመዘጋጀት ላይ እንዳሉ ተናግረዋል፡፡

የፓርቲው ማኅተም ከጠፋ በኋላ ሕገወጥ ተግባራት እንደሚፈጸምበት በመሥጋት፣ ከመስከረም 19 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ማንኛውም የፓርቲው ማኅተም ያረፈበት ዶክመንት ሕገወጥ መሆኑን መግለጻቸውን አቶ ይልቃል አስታውሰዋል፡፡( ምንጭ ሪፖርተር)