ኢትዮጵያና ሱዳን በአባይ ጉዳይ ላይ ያላቸው የጋራ ተጠቃሚነት አቋም ተጠናክሮ ይቀጥላል-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር

ኢትዮጵያና ሱዳን በዓባይ ጉዳይ ላይ ያላቸው የጋራ ተጠቃሚነት አቋም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለፀ።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሱዳን ምክትል ፕሬዝዳንት ሃሳቡ ሙሃመድ አብዱልራሂምን በጽህፈት ቤታቸው ዛሬ ተቀብለው አነጋግረዋል።

በውይይታቸው ሁለቱ አገሮች ያላቸውን ሁለንተናዊ ግንኙነት የበለጠ በሚያጠናክሩባቸው ጉዳዮች ላይ መክረዋል።

በተለይም በዓባይ ወንዝ የጋራ ተጠቃሚነት ላይ ያላቸው ግንኙነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው ከውይይቱ በኋላ ሁለቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት የገለፁት።

በኢትዮጵያ የታላቁ ሕዳሴ ግድብና በአባይ ወንዝ የጋራ ተጠቃሚነት ላይ ሁለቱ አገሮች ግልጽ አቋም ያላቸው ሲሆን፤ ግድቡ ሱዳንን ጨምሮ ለሌሎች ጎረቤት አገሮች በርካታ ጥቅሞች ያስገኛል።

ሁለቱ አገሮች በአካባቢያዊ ፀጥታና ሌሎች የጋራ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ትብብር የበለጠ በሚያሳድጉባቸው ሁኔታዎች ላይ መክረዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን እንደገለጹት፤ በአገሮቹ መካከል ያለው ግንኙነት በጋራ የያዟቸውን እቅዶች ለማሳካት ወሳኝ ነው።

ከዚሁ ጎን ለጎንም ሁለቱ አገሮች በቀጣናው ያሉትን ችግሮች እልባት ለመስጠት ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወቱ ተገልጿል።

የሱዳኑ ምክትል ፕሬዝዳንት ሃሰቡ ሙሃመድ አብዱልራሂም በበኩላቸው፤ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመረኮዘ መሆኑን አስረድተዋል።

በተለይም በኢኮኖሚ፣በመሰረተ ልማትና በጎረቤት አገሮች ፀጥታ ጉዳይ ላይ ያላቸው አቋምና ትብብር ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አመልክተዋል።

ሁለቱ አገሮች በአየር ትራንስፖርት፣ በመንገድ፣ በባቡር፣ በወደብ ፣ በኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት፣ በውሃና በሌሎች መሰረተ ልማቶች ያላቸውን ግንኙነት በማጠናከር ላይ ናቸው- (ኢዜአ) ።