ኢትዮጵያ የአፍሪካ አገሮች ነጻ የንግድ ቀጣናን እንደማትቀበል አስታወቀች

ኢትዮጵያ አህጉራዊው ነፃ የንግድ ቀጣና በአገር ኢኮኖሚና በህዝቦች ላይ የሚያመጣውን አሉታዊ ተጽዕኖ ግምት ውስጥ በማስገባት እንዳልተቀበለችው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ገለፁ።

አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናውን ተግባራዊ ለማድረግ 48 አገሮች የተስማሙ ሲሆን፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት አገሮች ግን አልተስማሙም ተብሏል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም በአዲስ አበባ የተካሄደውን 29ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ መጠናቀቅ አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

አህጉራዊው ነጻ የንግድ ቀጣና በሚመሰረትበት ወቅት በአገልግሎቶች ብቻ ሳይሆን በዕቃዎች ላይ የሚጣሉ ታሪፎች የተመጣጠኑና "ለንግድና ኢንቨስትመንት የተመቻቹ መሆን አለባቸው" ብለዋል።

ስለሆነም አጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና በፍጥነት መክፈት በአገሪቷ ኢኮኖሚና ህዝቦቿ ላይ ሊያደርስ የሚችለው አሉታዊ ተጽዕኖ ግምት ውስጥ መግባቱን ጠቁመዋል። በዚህ ምክንያት አለመቀበሏን ነው የተናገሩት።

ይሁንና "ኢትዮጵያ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ከአፍሪካውያን ጋር በንግድና ኢንቨስትመንት በጋራ ትሰራለች" ብለዋል።

አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናው እ.ኤ.አ በ2012 አዲስ አበባ በተካሄደው 18ኛው የመሪዎች መደበኛ ጉባዔ ላይ መሪዎች የመሠረቱት ሲሆን፤ ይህም ስምምነት እ.ኤ.አ በ2018 ላይ ወደ ስራ ይገባል ተብሎ ይጠበቃል።

በዚህም ከአንድ ቢሊዮን የሚበልጡ የ55 አገሮች ህዝቦችን ወደ አንድ የሚያመጣና ከሦስት ነጥብ አራት ትሪሊዮን ዶላር በላይ የሚገመት አጠቃላይ የአህጉሪቷ ምርት በንግድ ትስስሩ ላይ እንደሚቀርብ ከሕብረቱ የተገኘ መረጃ ያመለክታል። 

በነጻ ቀጣና ተግባራዊ በመሆኑ ላይ ካልተስማሙት መካከል ከኢትዮጵያ ሌሎቹ  ይፋ አልሆኑም። (ኢዜአ)